የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ቀዳማዊ የአማርኛ...

14
1 ቁጥር -ግንቦት ፪ሺህ ዓመተ ምሕረት ሰላምና ጤና ይብዛላችሁ፤ በዚህ ስርጭት ሦስት አጫጭር መጣጥፎች አቅርቤአለሁ። የተጀመሩት ተከታታይ ጽሑፎች በተከታዩ ስርጭት ይቀጥላሉ። የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ባለፉት 11 ዓመታት እየሠራሁ ስላለሁትና የጌታ ፈቃድ ቢሆን በቀጣዮቹ ጥቂት ዓመታት እንዲያልቅ ለምመኘው ሥራ ጸሎትን የሚጠይቅና በአጭር የሚያስተዋውቅ ነው። ቀዳማዊ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ዛሬ መጽሐፍ ቅዱስን በመጽሐፍ መልክ ማንበብ ብቻ ሳይሆን በኮምፒዩተር፥ በእጅ ስልካችን፥ ስንፈልግ እናነብበዋለን፥ ሲያሻን እንሰማዋለን፥ ቆርጠን ለጥፈን እንልከዋለን። ስለ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ እግዚአብሔር ይመስገን። ቃሉ ግን በቋንቋችን በቀላሉ የተገኘ አይምሰለን። ዛሬ በብዙዎቻችን እጅ ስላሉት ሳይሆን ከነዚህ ቀድሞ ስለተተረጎመውና የተሰራጨው ስለ መጀመሪያው የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉምና በሰፊውም ባይሆን እንመለከታለን። የተሰቀለው ክርስቶስ ክርስቶስን መስበክ ድንቅ ነው። ግን የቱ ክርስቶስ? ያልተሰቀለውን ኢየሱስ የሚሰብኩ እንዳሉ እናውቃለን? ጌታና አምላክ የሆነውን ክርስቶስ ሰውና ነቢይ ብቻ ነው። የተሰቀለው ኢየሱስ ሳይሆን እርሱን የሚመስል ሌላ ነው ለሚሉ መልስ አለን? የክርስቶስ መሰቀል፥ መሞትና መነሣት የተረጋገጠ እውነት ነው። የጳውሎስ የስብከቱ ማዕከል የተሰቀለው ክርስቶስ መሆኑ በመስቀሉ የተፈጸመውን ቤዛነት ለማጉላት ነው። መልካም ንባብ። ዘላለም መንግሥቱ / ዕዝራ ስነ ጽሑፍ። የዕዝራ ስነ ጽሑፍ አገልግሎት ግብና ዓላማ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረትና ይዘት ያላቸውን ቅዱሳንን የሚመግቡ ከአጫጭር መጣጥፎች እስከ ትልልቅ የማስተማሪያ መርጃዎች በማዘጋጀት ቤተ ክርስቲያንን መደገፍና በዚህም እግዚአብሔርን ማክበር ነው። የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ቀዳማዊ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ግንቦት ሺህ ዓመተ ምሕረት MAY 2014 [email protected] ቁጥር

Upload: others

Post on 12-Nov-2020

160 views

Category:

Documents


7 download

TRANSCRIPT

  • 1

    ቁጥር ፳፭ -ግንቦት ፪ሺህ ፮ ዓመተ ምሕረት MAY 2014

    ሰላምና ጤና ይብዛላችሁ፤

    በዚህ ስርጭት ሦስት አጫጭር መጣጥፎች አቅርቤአለሁ። የተጀመሩት ተከታታይ ጽሑፎች በተከታዩ ስርጭት ይቀጥላሉ።

    የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ባለፉት 11 ዓመታት እየሠራሁ ስላለሁትና የጌታ ፈቃድ ቢሆን በቀጣዮቹ ጥቂት ዓመታት እንዲያልቅ ለምመኘው ሥራ ጸሎትን የሚጠይቅና በአጭር የሚያስተዋውቅ ነው።

    ቀዳማዊ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ዛሬ መጽሐፍ ቅዱስን በመጽሐፍ መልክ ማንበብ ብቻ ሳይሆን በኮምፒዩተር፥ በእጅ ስልካችን፥ ስንፈልግ እናነብበዋለን፥ ሲያሻን እንሰማዋለን፥ ቆርጠን ለጥፈን እንልከዋለን። ስለ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ እግዚአብሔር ይመስገን። ቃሉ ግን በቋንቋችን በቀላሉ የተገኘ አይምሰለን። ዛሬ በብዙዎቻችን እጅ ስላሉት ሳይሆን ከነዚህ ቀድሞ ስለተተረጎመውና የተሰራጨው ስለ መጀመሪያው የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉምና በሰፊውም ባይሆን እንመለከታለን።

    የተሰቀለው ክርስቶስ ክርስቶስን መስበክ ድንቅ ነው። ግን የቱ ክርስቶስ? ያልተሰቀለውን ኢየሱስ የሚሰብኩ እንዳሉ እናውቃለን? ጌታና አምላክ የሆነውን ክርስቶስ ሰውና ነቢይ ብቻ ነው። የተሰቀለው ኢየሱስ ሳይሆን እርሱን የሚመስል ሌላ ነው ለሚሉ መልስ አለን? የክርስቶስ መሰቀል፥ መሞትና መነሣት የተረጋገጠ እውነት ነው። የጳውሎስ የስብከቱ ማዕከል የተሰቀለው ክርስቶስ መሆኑ በመስቀሉ የተፈጸመውን ቤዛነት ለማጉላት ነው።

    መልካም ንባብ።

    ዘላለም መንግሥቱ / ዕዝራ ስነ ጽሑፍ።

    የዕዝራ ስነ ጽሑፍ አገልግሎት ግብና ዓላማ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረትና ይዘት ያላቸውን ቅዱሳንን የሚመግቡ ከአጫጭር መጣጥፎች እስከ ትልልቅ የማስተማሪያ መርጃዎች በማዘጋጀት ቤተ ክርስቲያንን መደገፍና በዚህም እግዚአብሔርን ማክበር ነው።

    የመጽሐፍ ቅዱስ

    መዝገበ ቃላት

    ቀዳማዊ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ

    ግንቦት ፪ ሺህ ፮ ዓመተ ምሕረት MAY 2014

    [email protected]

    ቁጥር ፳፭

  • 2

    ቁጥር ፳፭ -ግንቦት ፪ሺህ ፮ ዓመተ ምሕረት MAY 2014

    ቀዳማዊ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ

    ዛሬ ጠዋት (April መጀመሪያ) በውስጣቸው የተነበበ የአማርኛ አዲስ ኪዳን የተጫነባቸው በፀሐይ ብርሃን ወይም በባትሪ ካስፈለገም በኤሌክትሪክ ኃይል፥ ይህ ሁሉ ከሌለ ደግሞ በእጅ እየተዘወረ የሚሠሩ ሁለት የታሸጉ Proclaimer ወይም አዋጅ ነጋሪ የተባሉ 'ሬድዮዎች' ወደ አገር ቤት እንድልክ በስጦታ ደረሱኝ። ሬድዮ ያልኳቸው ስማቸውን ስለማላውቅ ነው፤ ሞገድ የሚቀበሉ ሬድዮዎች ሳይሆኑ የተጫነባቸውን 'ዲጂታል' ድምጽ ብቻ የሚያጫውቱ ሬድዮ መሳይ ነገሮች ናቸው። Faith Comes By Hearing የሚባል ወንጌላዊ ድርጅት አሠርቶ የሚያዘጋጃቸውና የሚያድላቸው፥ ፈቃደኛ ሰዎችም እየገዙ የተለያዩ ቋንቋዎች መጽሐፍ ቅዱሶች ወይም አዲስ ኪዳኖች እንዲጫንባቸው አስደርገው የሚያድሏቸው ወይም የሚልኳቸው የወንጌል ማሰራጫዎች ናቸው። አሁን ከ800 በላይ በሆኑ ቋንቋዎች በድምጽ የተቀረጸ አዲስ ኪዳን አዘጋጅተዋል። ወንጌልን ለማሮጥ የሚተጉ ሰዎች ያስገርሙኛል።በተለይ ለማያውቋቸው ሰዎች ቃሉ በሚሰሙት፥ በሚያውቁት ቋንቋቸው እንዲደርሳቸው ግድ በሚላቸው ሰዎች እደነቃለሁ።

    መጽሐፍ ቅዱሳችንን በማንበብና በመስማት ክርስቲያኖች ሁሉ እንደሰታለን። ቃሉ የነፍሳችን ቀለብ ነው። እግዚአብሔርም ሕያው ቃሉን በእጃችን እንዲገኝ ስላደረገ ማመስገን አለብን። ግን ይህ የተገኘበት ሂደት ቀላል አለመሆኑን መገንዘብ አለብን። ዛሬ በኮምፒዩተራችን፥ በእጅ ስልካችን፥ በጥቃቅን የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎቻችን ሁሉ ሳይቀር፥ በጣታችን ነካ አድርገን ወይም በድምጽ አዝዘን መጽሐፍ ቅዱስን የምናነብበው ወይም የምንሰማው ብዙዎች ነን። ከአንድ በላይ ቋንቋ አማርጠን ማየትና ማንበብ፥ ማንበብ ካልቻልንም መስማት እንችላለን። ስለ ዘመናዊ ቴክኖሎጂም እግዚአብሔርን እናመስግን።

    መጽሐፍ ቅዱሳችን የተተረጎመልንና በእጃችን ሊሆን የቻለው እንዲህ በቀላለ አለመሆኑን ደግሞ ማስተዋል አለብን። የመጀመሪያው የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ መቼ በማን እና እንዴት እንደተተረጎመና የጣሩትና ተሳታፊዎቹ እነማን መሆናቸውን የምናውቅ ብዙዎች አይደለንም። ይህንን ማወቅ የተገባ ነው። በብዙዎቻችን እጅ የሚገኘው የ1954ቱ የቀድሞው ወይም የቀኃሥ ትርጉም የሚባለው ነው። ይህ ግን የመጀመሪያው የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ አይደለም። በዚህ መጣጥፍ ስለ መጀመሪያው ወይም መጀመሪያዎቹ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጓሜና ሰፊና ጥልቅ ጥናት የተደረገበት ሥራ ሳይሆን ለመንደርደሪያ የሚሆኑ ጥቂት ቃርሚያዎች ልጽፍ እወድዳለሁ። ይህ ሌሎች በዚህ አቅጣጫ እንዲጽፉ ለማነሣሣትና ለማበረታታት ይሁን።

    በአገራችን ብቻ ሳይሆን በተለያዩ አገሮችም መጽሐፍ ቅዱስ ወደ ሕዝባዊ ቋንቋ እንዲተረጎም የጣሩት ከቤተ ክርስቲያን መሪዎች ይልቅ ተርታ ክርስቲያኖችና የወንጌል መልእክተኞች መሆናቸው ታሪኩን ይበልጥ ተወዳጅ ያደርገዋል። በአንጻሩ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ በሕዝብ ቋንቋ ከቶም እንዳይኖር ብቻ ሳይሆን ሲኖርም እንዲጠፋ፥ ካልሆነም እንዳይሰራጭ እንቅፋት የሚሆኑት የነባሯ ቤተ ክርስቲያን ካህናት ሲሆኑ ያስደነግጣል። በአገራችንም የመጀመሪያው አማርኛ በውጪ ተተርጉሞ ከታተመም በኋላ ወደ አገር እንዳይገባና እንዳይሰራጭ ቤተ ክህነት እንቅፋት መሆኗ ወደ ጎን መተው የሌለበትና ትምህርት ልንቀስምበት የተገባ ታሪክ ነው። ይህ በአገራችንም በሌሎች አገሮችም፥ በተለይም በአውሮጳ በመካከለኛው ዘመን የታየ እውነት ነው። የመጽሐፍ ቅዱስ ጠባቂ የሚመስሉ ጠላቶች ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲፈልቁ መቼም ያሳዝናል። ስለ መጀመሪያው የእንግሊዝኛና ስለመጀመሪያው የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱሶች ትርጉም በትንሹ ልጻፍ።

    ኢትዮጵያ በትውፊትና በአገራዊ ታሪክ ቀደምት ብሉይን፥ ደሃራይ ደግሞ ሐዲስን የተቀበለ ሕዝብ አገር መሆኗ በስፋት ይነገርላታል። የብሉይ

    ተቀባይ መሆኗ ከትውፊት ያለፈ ተጨባጭ ማስረጃ የለውም። በቁፋሮ የተገኙና ከቋሚ ሐውልቶችና የቅርጽ ቅርሶች የሚገኙትም ማስረጃዎች ከክርስትና በፊት ሕዝቡ በብሉይ ኪዳን የተገለጠውን ፈጣሪ አምላክ አምላኪዎች መሆናቸውን አያሳዩም። ይልቅስ በተቃራኒው አለመሆኗን የሚያሳዩ አመልካቾች አሉ። እነዚህ አመልካቾችና ማስረጃዎች የሚያሳዩት ሕዝቡ ጨረቃና ፀሐይን፥ እንዲሁም ባሕርን ሰማይንና የብስን የሚያመልኩ አረማውያን መሆናቸው ነው። ምናልባት በዘመናት ውስጥ በሆነው በአይሁድ ብተና የተሰደዱ ጥቂት አይሁድ ወይም የአይሁድን እምነት የሚከተሉ ሰዎች ወይም የእምነቱ አድናቂዎች ሊኖሩ ይችላሉ ተብሎ መገመት ቢቻልም ጥንታዊቷን ኢትዮጵያ ብሔራዊ የሆነ አይሁዳዊ እምነት የናኘበት አገር አድርጎ መገመት የዋኅነት ነው።

    ክብረ ነገሥትስ? የሳባ ንግሥትና የሰሎሞን ታሪክስ? ሳባ ኢትዮጵያ መሆኑ የታወቀና የተረጋገጠ ለመሆኑ የሚቀርቡት አስረጅዎች ጥንታዊነትና አርኪነት ይጎድላቸዋል። ከቀይ ባህር ማዶ ለመሆኑ ግን አጥጋቢ ሰነዶች ይቀርባሉ። ይህ ሳባ የኛው ሳባ እንደሆነ አድርገን ብንወስድ እንኳ ከብሉይ ኪዳን የሳባ ንግሥት አምና መመለሷን የሚናገር ትውፊት እንጂ ታሪክ የለም። ታሪክን እንደ ታሪክ መተረክ አንድ ነገር ሲሆን ክፍተቱን በምናብ ጠቅጥቆ መሙላት ግን ሌላ ነገር ነው። ክብረ ነገሥት የተጻፈው ወይም የተተረጎመው ወይም እስከ ጭራሹ የተፈጠረው ታሪኩ ከሆነበት ከ2ሺህ ዓመታት በላይ ቆይቶ ነው። ሰሎሞን የኖረው ከልደተ ክርስቶስ ሺህ ያህል ዓመታት በፊት ሲሆን ክብረ ነገሥት ብቅ ያለው ከልደተ ክርስቶስ በኋላ በ13ኛው ምዕት ዓመት ነው። የተጻፈበትን ዘመን መልክ ስንመረምር ደግሞ ማኅበራዊ፥ ስነ ልቡናዊና በተለይም ፖለቲካዊ ግፊት እንዳለበት በጉልህ ይታያል። ስለዚህ አሳብ በዕዝራ ቁጥር 7 እና 8 በመጠኑ ጽፌአለሁ። እርግጥ በብሉይ ኪዳን የምናገኛቸው ጥቂት የአይሁድ ደንቦች እንደ ባህል እና ወጎች ወይም ተጋቦት ሆነው በአገሪቱ መገኘታቸው የታወቀ ነው። ባህል ደግሞ የሚወራረስና የሚተላለፍ ነው። እነዚህ ብቻ ሳይሆኑ የሌሎች አሕዛብ ባህሎችም በሕዝቡ ውስጥ በስፋትና በጥልቀት ይገኛሉ፤ ከአንዱ ወደ ሌላው ይተላለፋሉ። ደግሞም፥ 'እነዚህ ባህሎች ልማዶችና ባህሎች ናቸው ወይስ ደንብና ሕጎች ናቸው?' የሚለው ጥያቄ ጠቃሚና መጤን ያለበት ነው። በተጨማሪም እነዚህ ባህሎች መቼ ተጀመሩ? የሚለውም አስፈላጊ ጥያቄ ነው። ብሉይ ኪዳን ለአይሁድ በተሰጠበት መልኩ ግን መጽሐፍ ቅዱስ በአገሪቱ ከመገኘቱ አስቀድሞ አለመኖሩን፥ ቢያንስ በመንግሥትና በብሔር ደረጃ ሕጋዊ አካልን ተላብሶ ያለመገኘቱን መናገር ይቻላል።

    ብሉይ ኪዳን በኢትዮጵያ ኖረ ከተባለ ከግዕዝ በፊት በነበረው በሳባ ፊደልና ቋንቋ ተተርጉሞ ነበር ማለት ነው። ያለዚያ ደግሞ በዕብራይስጥና በሱርስጥ ወይም አራማይስጥ በተጻፈበት መልኩ ነበረ ማለት ነው። እነዚህ ቋንቋዎች በአገሪቱ በየትኛውም ዘመንና ቦታ አልነበሩም። ቤተ እስራኤል በሚባሉት ዘንድም እንኳ ዕብራይስጥና አራማይስጥ በጽሑፍም ሆነ በንግግር መልኩ ከቶም አልኖረም፤ በሚታወቀው ታሪካችን ውስጥ ኖሮም አያውቅም። እንግዲህ ብሉይም ሆነ አዲስ ኪዳናት በግዕዝ ቋንቋ የተተረጎመው በኋለኞቹ ዘመናት ነው ማለት ነው።

    የግዕዝ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ልጽፍ የተነሣሁት ስለ አማርኛው የመጀመሪያ መጽሐፍ ቅዱስ ቢሆንም ስለ ግዕዙም ጥቂት ልበል። የግዕዝ መጽሐፍ ቅዱስ በትክክል መቼ እንደተተረጎመ እርግጠኛ የሆነ የተረጋገጠና ይፋ የሆነ ሰነድ መኖሩን አላውቅም። ስለ ግዕዝ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም የተጻፈ አንድ መጽሐፍ እንዲህ ይላል፤ "የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን በተመለከተ ሰሎሞንን በጎበኘችው በንግሥተ አዜብ ዘመን ከዕብራይስጥ ወደ ግዕዝ ተተረጎሙ። በዚህም ምክንያት በብሔረ አግዓዚ (ኢትዮጵያ) የሚገኙ የነቢያት

  • 3

    ቁጥር ፳፭ -ግንቦት ፪ሺህ ፮ ዓመተ ምሕረት MAY 2014

    መጻሕፍት ትርጉም የጠራ ሆነ። ከልደተ ክርስቶስ በፊት ሕዝቡ ለአይሁድ ኃይማኖት ታማኝ ነበሩ።" 1 በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጻፈችውን የሳባን ንግሥት ኢትዮጵያዊትነት የሚያምኑት እንደዚህ ከላይ የተጠቀሰው አሳብ እንደተጻፈበት መጽሐፍ አነጋገር ብሉይ ኪዳን በዚያን ጊዜ ወይም ከዚያ ብዙም ሳይቆይ እንደተተረጎመ ይገምታሉ። ይህ ግምት አንድ ብቻ ችግር አለበት። ያ ችግር ግን ችግር ነው። ያም በዚያን ዘመን የግዕዝ ቋንቋ ራሱም አለመኖሩ ነው። ከዚያ ዘመን እስከ ብዙ መቶ ዓመታት ቆይቶም ቋንቋውም ፊደሉም ሳባዊ ነበረ። በዚያ ፊደል ደግሞ በብራና የተጻፈም ሆነ በዓለት ላይ የተወቀረ አንድም የብሉይ ኪዳን ጥቅስ ኖሮ አልተገኘም። እንደሚባለው ኢትዮጵያ ቀደምት ብሉይን፥ ደሃራይ ደግሞ ሐዲስን የተቀበለ ሕዝብ አገር ኖራ ብትሆን በሳባ የተጻፈ ኦሪት እንኳ በኖረ ነበር። ሲሆን ሲሆን በብዛት መገኘት ነበረበት። ግን በጥቂትም ብቻ ሳይሆን ከቶም የለም።

    በአለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በመዝገበ ቃላትና ሰዋሰው መጽሐፍ መግቢያ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ወደ ግዕዝ መመለስ ብሉይ ከሰባ ሊቃናት ትርጉም የተቀዳ መሆኑ ተጽፎአል። ይህ ምንጩን እንጂ ዘመኑን አይናገርም። ብሉይ ከልደተ ክርስቶስ በፊት ከዕብራይስጥ ወደ ግዕዝ ተመለሰ ማለት ግን የማይመስል ነገር መሆኑን፥ ". . . ብሉያችን በዘመነ ብሉይ ከዕብራይስጥ ተመልሷል ማለት በነብሪድ ይስሐቅ እጅ ሳይከካና ሳይቦካ ሳይጋገር ምጣድ ሳይነካ እምኀበ አልቦ የተገኘ የሐሳብ የምኞት የሕልም እንጀራ ነው።" ይላሉ። ቀጥሎም ብሉይ ከሐዲስ ጋር ወደ ግዕዝ የተመለሰው በዘመነ ሐዲስ በከፊል በፍሬምናጦስ እንደሆነ፥ "የመለሳቸውም ዕብራዊ፥ ሌዋዊ ወይም ግብጻዊ ያይዶለ ጽራኣዊውና ጢሮሳዊው ፍሬምናጦስ ነው። . . . የቀረውም ብሉይ ከላስቶች መንግሥት በኋላ ብርሃነ አዜብ በተባለው በካልእ ሰላማ ከዐረብ ቋንቋ ተመልሷል።" ሲሉ ጽፈዋል።2

    እንደ ኪዳነ ወልድ አመለካከት ብሉይ ከሐዲስ ጋር ክርስትና ወደ ኢትዮጵያ ገብቶ ከቆየ በኋላ ነው የተተረጎመው። የሰባ ሊቃናት ትርጉም የሚባለው የብሉይ ትርጉም ከልደተ ክርስቶስ በፊት በ3ኛው መቶ ተጀምሮ በሁለተኛው መቶ ያለቀ ብሉይ ኪዳን ከዋና ቋንቋ ከዕብራይስጥ ወደ ሕዝባዊ ግሪክ (ኮይኔ ወይም መደዴ ግሪክ) የተመለሰበት ነው። ይህንን ትርጉም በእስክንድርያ ላለው ቤተ መጻሕፍቱ እንዲጨመር ዳግማዊ በጥሊሞስ ፍላደልፍ ነው ያስተረጎመው። እዚህም አስገራሚው ነገር የእግዚአብሔር ቃል በሕዝብ ቋንቋ እንዲተረጎም አድራጊው የእግዚአብሔር ካህናት ሳይሆኑ ለቤተ መጻሕፍቱ ማደርጃ ቢሆንም እንኳ አረማዊ ንጉሥ መሆኑ ነው። የግዕዙ ትርጉም ከዕብራይስጥ ይልቅ ከግሪኩ የሰባ ሊቃናት እና የዐረብኛ ትርጉም መወሰዱ እንጂ ምንጭ ቋንቋ አለመተርጎሙን ያስተዋለ ጀርመናዊ ሊቅ ሲዲ ጳውሎስ ለጎንደር ሊቃውንት፥ "ብሉያችኹን ከዕብራይስጥ፥ ሐዲሳችኹን ከጽርእ እያስማማኹ አርሜ ንባቡን ከነትርጓሜው አሳትሜ ብዙ መጻሕፍት ላምጣላችሁ ቢላቸው አንፈልግም ብለው በምቀኝነት እንዳስቀሩት ቅንነት ያላቸው ብዙ ሰዎች ይተርኩታል፤ ርሱም በታሪኩ ጥፎታል ይባላል።"3 እንደ በጥሊሞስ ፍላደልፍ ያሉ አረማውያን ቃሉ ከምንጩ በሕዝቡ ቋንቋ እንዲተረጎም ሲያደርጉ ሊቃውንትና ካህናት ደግሞ እንዳይተረጎም በር ይዘጋሉ።

    ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ያነብብ የነበረው የየትኛውን ቋንቋ መጽሐፍ ነበር? ይህ ይሁዲ ጃንደረባ የአገር ሰው ከመሰኘት ይልቅ ኢትዮጵያዊ ዜጋ የተደረገ ወይም የሆነ አይሁዳዊ ልደት ያለው ሊሆን ይችላል። ብዙ ጊዜ ጃንደረባ ወይም ስልብ ተደርገው፥ አንዳንዴ ሳይደረጉም በቤተ መንግሥት የሚያገለግሉት የተማረኩ ወይም ያለምርኮ በሌላ መንገድ የተወሰዱ እውቀትና ጥበብ ያላቸው ሰዎች ናቸው። ኋላ ክርስትና ወደ

    1 ቀ/ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል፥ ገጽ 16። 2 ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፤ ገጽ 16-18። 3 ከላይ የተጠቀሰው፤ ገጽ 19።

    አክሱም በገባ ጊዜ አዲስዮስ እና ፍሬምናጦስ በቤተ መንግሥት ኖረው እንዳገለገሉት ማለት ነው። ይህ ሰው በግዕዝ ወይም በሳባይስጥ ሳይሆን በዕብራይስጥ የተጻፈ ጥቅልል ነው ያነብ የነበረው። ዕብራይስጥ ካልሆነም ምናልባት የሰባ ሊቃናቱ የግሪክ ትርጉም ለመሰራጨት በቅቶ ከሆነ ያንንም ሊሆን ይችላል። ከግሪክ ይልቅ ግን ዕብራይስጥ ይመስላል። የዕብራይስጥ ጽሑፍ ያነብ እንደነበር የምንረዳው ታሪኩ በተጻፈበት በሐዋ. 8 ፊልጶስ ሲያነብ ከነበረበት መጽሐፍ ጀምሮ ስለ ኢየሱስ ወንጌልን እንደሰበከለት በመጻፉ ነው። ፊልጶስ አይሁዳዊ ነውና ቋንቋው ዕብራይስጥ ነው። ብሉይ ኪዳንም የተጻፈው በዚሁ ቋንቋ ነው። የፊልጶስ አይሁዳዊነት የግሪኩን ቋንቋ ለዚህ ንባብ ተመራጭ አያደርገውም።

    በፍሬምናጦስና ተባባሪዎቹ ካልተተረጎመ የግዕዝ መጽሐፍ ቅዱስ ከኬልቄዶን ጉባኤ (451 ዓ. ም.) በኋላ ስደትን ሸሽተው ወደ ኢትዮጵያ የተጠጉ በታሪክ ተሰዓቱ ቅዱሳን እየተባሉ የሚጠሩት ቋንቋውን ተምረው ወይም ከአገር ሊቃውንት ጋር እንደተረጎሙትም ይገመታል። ይሁን እንጂ ግን ማን ወይም እነማን፥ ከየትኛው የምንጭ ቋንቋ፥ መቼ፥ በምን ሂደትና ምን ያህል ጊዜ ፈጅቶ እንደተተረጎመ ግልጽ ሆኖ የሚታወቅ በማስረጃ የተደገፈ ዘገባ የለም። ክርስትና በይፋ ወደ አገሪቱ እንደገባ የሚታወቀው በ4ኛው መቶ የመጀመሪያ አጋማሽ ቢሆንም ወዲያው ተተረጎመ ማለት አይቻልም። በአገር ወይም መንግሥት ደረጃ ሃይማኖቱ ሲጠናከር ግን ይህ እንደተደረገ ይታመናል። በኅትመት ደረጃ በ16ኛው መቶ በቫቲካን በተገኙ ኢትዮጵያውያን መነኮሳት የተዘጋጀ የግእዝ መዝሙረ ዳዊትና አዲስ ኪዳን መኖራቸው እንጂ ታትመው ስለመሰራጨታቸው አይታወቅም። የዚህ ትርጉም ወይም ኅትመት ውጤት የአማርኛው መጽሐፍ ቅዱስ በእንግሊዝ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር አማካይነት በሚዘጋጅበት ወቅት ታትሞ ወደ አገር ውስጥ ገብቶ እንዲሰራጭ ጥረት ተደርጎ ነበር።

    የአማርኛ ትርጉሞችና ቀዳሚው ትርጉም ብዙ የሚታወቀው እና በብዙኃኑ እጅ የሚገኘው የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም በኛ አቆጣጠር የ፲፱፻፶፬ቱ ትርጉም (የቀድሞው ትርጉም ወይም የቀኃሥ ትርጉም የሚባለው) ነው። የዚህ ትርጉም ሥራ ራሱን የቻለ ታሪክ ያለው ተጀምሮ፥ በጣሊያን ወረራ ምክንያት ተቋርጦ፥ ከድል በኋላ ተቀጥሎ ያለቀ ከ30 ዓመታት በላይ የፈጀ ሥራ ነው። ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ገና አልጋ ወራሽ ሳሉ ሥራው ተጀምሮ የተጠናቀቀው በ1940ዎቹ መጨረሻ ሆኖ የታተመው በ50ዎቹ አጋማሽ ነው። ይህ በጣሊያን ወረራ ከመቋረጡ በፊት የተሠራው ያላለቀ ትርጉም አዲስ ኪዳኑ በኢጣልያ ወረራ ጊዜ እንደ ምንም ወጥቶ በእንግሊዝ አገር 'የባክስተን ትርጉም' (The Buxton Bible) ተብሎ ታትሞ በጥቂቱ ተሰራጭቶ ነበር። ንጉሡም ያነብቡት የነበረው የአማርኛ እትም ይህ ነበር ይባላል። የታተመው በ2ኛው የዓለም ጦርነት ጊዜ በመሆኑ ለንደን በጀርመን አውሮፕላኖች ስትደበደብ ይህ ኅትመትም በተከማቸበት ሊወድም በቅቶአል። የባክስተን ትርጉም የተባለው አልፍሬድ ባክስተን የተባለው እንግሊዛዊ በጣሊያን ሥር ከነበረችው ኢትዮጵያ በጅምር የቀረው ትርጉም ወጥቶ ወደ እንግሊዝ እንዲሻገር ስላደረገ ነው። ይህ ትርጉም ክለሳ የሚያስፈልገው መናኛና በፍጥነት የተሠራ ይመስላል፤ ኋላ በአሜሪካን አገር እንደገና በቄስ ዶናልድ

  • 4

    ቁጥር ፳፭ -ግንቦት ፪ሺህ ፮ ዓመተ ምሕረት MAY 2014

    ባርንሃውስ የማሳተሚያ እርዳታ ሰብሳቢነት ታትሞ ነበር፤ ግን ጥቂት ያልሆኑ ግድፈቶችና የሕትመት ስሕተቶችም ተገኝተውበታል። በጉልህ የሚታወቀው ስሕተት ከላይ ባለው ገጽ ያሳየሁት ራእ. 19፥10 እና 22፥9 ላይ ያለው 'እንዳታደርገው ተጠንቀቅ' የሚለውን 'እንድትሰግድልኝ ዕወቅ' ተሰኝቶ የተተረጎመው ነው። አተረጓጎሙ የስሕተት መሆኑ ከዐውዱ ይነበባል። ግን በመላእክት ስግደት ለታፈነው ሕዝባችን አወናባጅ ስሕተት ነው። ይህ ትርጉም ስሕተቱ እንደታወቀ ወዲያውኑ ከስርጭት እንዲታገድ ተደረገ።

    ከ፲፱፻፶፬ቱ ትርጉም በኋላ 'አዲሱ ትርጉም' ወይም 'ቀለል ባለ አማርኛ የተተረጎመ' የተሰኘው፥ ከዚያ ቀጥሎ ደግሞ 'ሕያው ቃል' ተሰኝቶ Living Bible በተባለው የእንግሊዝኛ አተረጓጎም መንገድ የተመለሰው፥ በቅርቡ ደግሞ 'መደበኛ ትርጉም' የተባለው የእንግሊዝኛው የNIV Bible ትርጉምና ማብራሪያው ታትመዋል። የመጀመሪያው የአማርኛ ትርጉም ግን ከነዚህ ትርጉሞች ከመቶ ዓመታት በፊት የተሠራ ተወዳጅ ታሪክ ያለው ነው። የግዕዝ ቋንቋ የሕዝብ ቋንቋነቱ ቀርቶ የቤተ ክህነት ቋንቋ ከሆነም በኋላ መጽሐፍ ቅዱስን ለሕዝብ በሚገባ ቋንቋ በአማርኛ ብቻ ሳይሆን በሌሎቹም ቋንቋዎች መተርጎምን ከቶም ከቁጥር አለማስገባት እንደ ሮማዋ ቤተ ክርስቲያን ሁሉ የኢትዮጵያም ሊቃውንትና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ትልቅ አስወቃሽ ነጥብ ነው። ከሺህ አምስት መቶ ዓመታት በላይ በሆኑ ዘመናት ወንጌል በሕዝብ ቋንቋ እንዲነበብ የተደረገ አንድም የትርጉም ሥራ አለመኖሩ ከአሳፋሪም በላይ ነው።

    በአውሮጳ የሮማይስጥ (ላቲን) ቋንቋ እንደኛው ግዕዝ በአንድ ዘመን መንግሥታዊ ወሕዝባዊ ቋንቋ ነበረ። የመንግሥቱ መፍረስና ተበትኖ መብዛት የየብሔሩን ቋንቋዎችን ሲያጠናክር ራሱ ሮማይስጥ ግን እንደ ሕዝብ ቋንቋ አልቀጠለም። ቤተ ክርስቲያን (ካቶሊካዊት) ግን ቋንቋውን መጠቀሟን ቀጠለች። መልእክቱ ይሰማል? ሰዎች ይረዱታል? ይገነዘቡታል? ተብሎ ሊጠየቅለት የተገባው ሕዝቡ መሆኑ ቀርቶ ቋንቋው ራሱ የከበሬታው ትኩረት ሆነ። ስለዚህ በሮሜ ግዛተ ዐፄ መጽሐፍ ቅዱስ ሕዝብ በሚሰማው ቋንቋ እንዲተረጎም በመደፋፈር ፈንታ በተቃራኒው የትርጉም ሙከራዎች እንዳይኖሩ ብቻ ሳይሆን ሞካሪዎቹም እንዲጠፉ ይደረግ ነበር። ይህ የሚደረገው ደግሞ በመንግሥት ሳይሆን እንደ ተቋም በሆነችውና መንግሥትን የሚገዳደር ሥልጣን በነበራት ቤተ ክርስቲያን አማካይነት ነበር። መለኮታዊው ቃል፥ በተለይም አዲሱ ኪዳንና የመዳናችን ማኅተም የታተመበት ታሪክ ያለበት ወንጌሉ ለሰዎች በሚደመጥና በሚገባ ቃል ሊዳረስ መበረታታት የተገባው መሆኑ ቀረና በሌሎች ልሳናት የተተረጎሙት ትርጉሞች ብቻ ሳይሆኑ ሊተረጉሙ የጣሩ ተርጓሚዎችም ከትርጉሞቻቸው መጻሕፍት ጋር በእሣት እየተቃጠሉ እንዲቀጡ ይደረግ ነበር። ራሷ ማድረግ ወይም ማስደረግ ያለባትን ይህንን ነገር አለማድረጓ ሲያሳዝን ቃሉን የማዳረስ ሸክም በልባቸው ያደረ ቅዱሳን ይህን ሊያደርጉ በመጣራቸው ማድነቅና መባረክ የነበረባት ቤተ ክርስቲያን እነዚህን ሰዎች ከማውገዝ አልፋ በእሳት እያነደደች አስወገደቻቸው።

    ኋላ በ1611 የተተረጎመው ይፋ የእንግሊዝኛ ትርጉም (ኪንግ ጄምስ ቨርዥን የሚባለው) 80% ያህል የወሰደው ከቲንዴል ትርጉም እንደሆነ የሚታመነውን ቀዳሚ የእንግሊዝኛ መጽሐፍ ቅዱስ ወደ ሕዝቡ ቋንቋ የተረጎመው ዊልያም ቲንዴል ነው። ቲንዴል ይህን ማድረጉ፥ ማለትም መጽሐፍ ቅዱስን ሕዝብ በሚጠቀምበት የእንግሊዝኛ ቋንቋ መተርጎሙ ወንጀል ሆኖበት በቤተ ክርስቲያን ተወግዞ በ1536 በእሣት ተቃጥሎ ነበር የተገደለው። ቲንዴል በሚቃጠልበት እንጨት ተጠፍሮ ታንቆና በእሳት ተቃጥሎ በሚሞትበት ጊዜ ድምጹን ከፍ አድርጎ በጩኸት የጸለየው ቃል፥ "እግዚአብሔር ሆይ፥ የእንግሊዝን ንጉሥ ዐይኖች ክፈት" ብሎ ነበር። ጸሎቱ ተሰምቶ ነበር። መቶ ዓመት ሳይሞላ 'ኪንግ ጄምስ ቨርዥን' የሚባለውን ትርጉም የእንግሊዝ ንጉሥ ራሱ አስተባብሮ አስተረጎመ። ቤተ ክርስቲያን ሳትሆን ንጉሥ ጄምስ! እዚያ በጥሊሞስ ፍላደልፍ፤ እዚህ ንጉሥ ጄምስ፤ እኛጋ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ። ይደንቃል። ቲንዴል የተረጎመው እንደ ቋንቋ ሊቅነቱ ከምንጭ ቋንቋዎቹ ከዕብራይስጥና ግሪክ

    ነው። አንዳንድ የቃላት ትርጉሞቹ፥ ለምሳሌ፥ የግሪኩ 'ኤክሌሲያ' የሚለው ቃል ትርጉም በተለይም በዘመኑ የሰለጠነችውና ፖለቲካዊና ድርጅታዊ መዋቅር የሆነችው ቤተ ክርስቲያን አለመሆኗን ለማሳየት ቃሉን 'ቤተ ክርስቲያን' በማለት ሳይሆን 'ጉባኤ' በማለት መተርጎሙ የዘመኗን ቤተ ክርስቲያን በጣም ያበሳጨ ነበረ። ይህ የብስጭትና የክሳቸው መነሻ የት መሆኑን ያሳያል።

    ከቲንዴል በፊት ከ7ኛው መቶ ጀምሮ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች በተለያዩ ጊዜዎች በትንሽ በትንሽ ቁርጥራጭ ወደ ጥንቱ እንግሊዝኛ ተተርጉመዋል። የመጀመሪያውን ሙሉ የእንግሊዝኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም የተረጎመው ጆን ዊክሊፍ ነው። ዊክሊፍ ቄስ ያይደለ የዩኒቨርሲቲ አስተማሪ፥ ሰባኪና ተርጓሚ ነበረ። ሎላርድ ተብለው ከተጠሩ ጋር አብረው ሆነው ክህነትን የሚቃወምና መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ብቻ የሚያተኩር ስብከት ይሰብኩ ነበር። በዘመኑ ካህናት መንፈሳውያን የቃሉ ሰባኪዎች ሳይሆኑ ዓለማውያንና በምድራዊ ብልጽግና የሰከሩ ከበርቴዎች ነበሩ። የሎላርዶች ስብከት የቃሉ ሰባኪ አገልጋዮች ከምድራዊ ብልጽግና የተለዩ ይሁኑ፥ የሰማያዊው መንግሥት አዋጅ ነጋሪዎች ይሁኑ የሚልም ነበር። ሎላርድ ማለት የስድብ ስም ሆኖ ያልተማረ፥ ቢማርም በእንግሊዝኛ ብቻ የተማረ፥ ላቲንን የማያውቅ ማለት ነው። ይህ ስብከታቸው እና 'ቃሉ በሕዝብ ቋንቋ መተርጎም አለበት' የሚለውን በዘመኑ ይናኝ የነበረ አሳብ ይደግፉና ያሰራጩም ስለነበር በሮማዋ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እንደ ከሐዲ ተቆጥረው ተሰደዱ። የፕሮቴስታንት ንቅናቄ ጥንስስ ይህ የዊክሊፍ እና የሎላርዶች ንቅናቄ መሆኑን ታሪክ ጸሐፍት ይናገራሉ። አራቱን ወንጌላትና ምናልባት ጠቅላላውን አዲስ ኪዳን የተረጎመው ራሱ ዊክሊፍ እንደሆነ ሲታመን እርሱ ይህን ሲሠራ ሳለ ረዳቶቹ ሎላርዶች ደግሞ ብሉይ ኪዳንን እንደተረጎሙ ይገመታል። መጽሐፍ ቅዱስን የተረዳ ሰው በመሆኑ በክህነት፥ በጵጵስናና በምኩስና ዙሪያ ያሉትን ስሕተቶች አውግዞ ያስተምር ነበርና በዘመኑ ሁሉ ጥቃት ሲሰነዘርበት ኖረ። ይህ ሰው በ1384 መጨረሻ ሞተ። ሥራው ግን አልሞተም። እርሱን ብቻ ሳይሆን ሥራዎቹን ሁሉ ለማውገዝ ሲባል አጥንቱ ከተቀበረበት ተቆፍሮ ወጥቶ በዘመኑ ከሐዲዎች ተብለው የተፈረጁ እንደሚደረጉት እንዲቃጠል በሜይ ወር 1415 ተወሰነ። አጽሙ ከተቀበረበት ከ30 ዓመታት በኋላ ወጥቶ እንዲጋይ ተደረገ። በዚያው ሳምንት የዊክሊፍን ሥራ ያሰራጭ የነበረ ጃን ሃስ ክህነቱ ተገፍፎ እርሱም እንዲቃጠል ተፈረደበት። ይህን በግንባር ቀድማ ያደረገችውና ያስደረገችው ቤተ ክህነት ናት። አስፈጻሚዎቹም ካህናት ናቸው።

    ይህ ዊክሊፍ አጥንቱ ከመቃብር ወጥቶ የተቃጠለው ከፕሮቴስታንት ንቅናቄ መቶ ዓመት በፊት ሲሆን በዚያው የእርሱ አጥንት በተቃጠለበት ጊዜ በአገራችን ወደ መጽሐፍ ቅዱሳዊ እምነት እንመለስ የሚሉ ደቀ እስጢፋ የተባሉት ሰዎችም የተነሱበትና የከፋ ቅጣትን የተቀበሉበት ዘመንም ነበር። አንዱ መሠረታዊ ልዩነት ግን በአውሮጳ ውስጥ ቤተ ክርስቲያን ምድራዊውን መንግሥት የተቆጣጠረችበት ጊዜ ሲሆን በዚያን ጊዜ በአገራችን ደግሞ ቤተ ክርስቲያን በመንግሥትና በንጉሥ (ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ) መዳፍ ውስጥ የገባችበት ጊዜ መሆኑ ነው። ቤተ ክርስቲያን ቃሉ ለሕዝብ ጆሮ እንግዳ ሆኖ እንዲቀር ያደረገችውን ያህል ንጉሡም ይህንኑ አብዝቶ አደረገ እንጂ የተሻለ አልሠራም። በአገራችን ታሪክ አንዳንድ ንጉሦች መንፈሳዊነት ሲያይልባቸው፥ አንዳንዶች ደግሞ ቃሉ በእውነት ለሕዝብ በሕዝብ ቋንቋ መድረስ እንዳለበት ገብቶአቸው ይህ እንዲሆን ሲጥሩ ሌሎች ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን ራሷን የመግዣ መሣሪያ በማድረግ ጨለማ እንዲጠነክር መብራትን ሲያጠፉ ኖረዋል።

    ወደ አማርኛው ቀዳሚ ትርጉም ከመመለሴ በፊት ከዚህ ጋር የሚቀራረብ አንድ ነጥብ በእግረ መንገድ ላክል። በቲንዴል ዘመን ለቃሉ መሰራጨት ሳይሆን ለአንድ ግብ ወይም ዓላማ ዘብ የቆሙ ሰዎች እንደነበሩ ሁሉ፥ ለምሳሌ፥ ቤተ ክርስቲያን (ኤክሌሲያ) የሚለው ቃል ጉባኤ የሚለው ትክክለኛ ትርጉም ያስቆጣቸው እንደኖሩ በኛም አገር መኖራቸውን እናስተውል። በ1980ዎቹ መጀመሪያ በታተመው የአማርኛ መጽሐፍ

  • 5

    ቁጥር ፳፭ -ግንቦት ፪ሺህ ፮ ዓመተ ምሕረት MAY 2014

    ቅዱስ እትም (ያው የ፲፱፻፶፬ቱ ሆኖ የአዋልድ መጻሕፍትን ያካተተው 'በተለይ ለኢኦተቤ/ክ የታተመው' የተባለው) ብሉይ ኪዳን ከተቀጠሉበት የአዋልድ መጻሕፍትና ቅጥያዎች በቀር አንድ ሲሆን በአዲስ ኪዳን ውስጥ ግን የተጨመሩ ወይም የተሳጉ ጥቂት ኦርቶዶክሳዊ ቃላት አሉ። ለምሳሌ፥ ቄስ ወይም ቀሲስ፥ ሊቅ፥ ጳጳስ የሚሉት ቃላት የተደጋገሙ ናቸው። ይህ እትም በአዲስ ኪዳን ሽማግሌ የተሰኙትን ቃላት ቄስ ወይም ቀሲስ በማለት ተርጉሞታል። በግሪክ ፕሬስቡቴሮስ የሚለው ቃል ነው። በአማርኛ ቀሲስ ቄስ ወይም ካህን ተብሎ ይተረጎማል።4 ቲቶ 1፥5ን ከ1ጴጥ. 5፥1 ማስተያየት በጣም ጥሩ ምሳሌ ነው። ተርጓሚዎቹ ጥቅሱን “ቀሳውስትን” ብለው ተርጉመው በግርጌ ማስታወሻ “የግሪኩ ሽማግሌዎች ይላል” ብለው ጽፈዋል። ከየትኛው ነው የተረጎሙት ማለት ነው? አዲስ ኪዳን በመጀመሪያ የተጻፈበት ግሪኩ ይህን ካለ እነሱ ወይም አማርኛ ከምንጩ ቋንቋ ከግሪኩ መብለጣቸው ነው? የተገላቢጦሽ ግሪኩ የግርጌ ማስታወሻ፥ አማርኛው ደግሞ ዋና ሆነሳ! የግሪኩ አዲስ ኪዳንም የአማርኛው ትርጉም ሊቃውንትም “ሽማግሌ” ያሉትን፥ በኋላ የመጣው ተርጓሚ፥ “የግሪኩ ሽማግሌ ይላል፤ እኔ ግን ሊቅ፥ ሊቃናት፥ ቄስ፥ ቀሳውስት፥ ቀሲስ” ብዬዋለሁ ቢል ምን ይሉታል? ከተረጎሙት ደግሞስ ለምን መርጠው ለወጡት? ለምሳሌ ማቴ 15፥2ን “የቄሶችን ወግ ይተላለፋሉ” በማለት ፈንታ እንደነበረ፥ “የሽማግሎችን ወግ ይተላለፋሉ”ብለው ሲተዉት ሌላውን ክብር፥ ሹመት፥ ሞገስ፣ ሥልጣን ያለበት የመሰላቸውን ቄስ፥ ቀሲስ እያሉ ለውጠውታል። ለምን? ይህን የለወጠው ሰው ቄስ ወይ ሊቅ ሆኖ ለቄስና ለሊቅ ጥብቅና የቆመ ይመስላል። አንድ ትርጉም ወይም ለውጥ ሲደረግ የአድራጊውን ማንነት መግለጡ የተገባ ሲሆን እዚህ አልተደረገም። የተገባ የሚሆነውም ያ ሰው የቋንቋ ሊቅነቱ እንዲፈተሽ ነው።

    ይህ የሚያሳየን ወደ አማርኛ ቀድሞ በካህናት ቢተረጎም ኖሮ እንኳ ምን መሳይ፥ ወደማን የሚያመለክትና ማንን ያማከለ ትርጉም ሊሆን እንደሚችል ነው። ያም ሆኖ ከቶም የቅዱሣት መጻሕፍት ትርጉም ሥራ በመደዴው ሕዝብ ቋንቋ ሊደረግ አልተሞከረም። የ፲፱፻፶፬ቱ ትርጉም አስጀማሪም ቤተ ክርስቲያን ሳትሆን አልጋ ወራሹ ራስ ተፈሪ መሆናቸው፥ ያስጨረሱትም ራሳቸው መሆናቸው ሌላ ለነባሯ ቤተ ክርስቲያን አንገት የሚያስደፋ ታሪክ ነው። እንዲያውም ወደ አማርኛ የተተረጎሙት መጽሐፍ ቅዱሶች ወደ አንባቢ እጅ እንዳይደርሱ ከአቡንና ከእጨጌ እስከ ካህናት ድረስ ቤተ ክህነት ተጻራሪ ሆና መቆየቷን የመጀመሪያውን የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ያሳተመው የእንግሊዝ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ዘገባዎች ያመለክታሉ። እነዚህ ዓመታዊ ዘገባዎች የታሪክ ብልጽግናን የተጎናጸፉ ዘገባዎች ናቸው። እዚህ አንድ ሁለቱን ላውሳ፤

    በ20ኛው የChurch Missionary Society for Africa ጉባኤ ዘገባ የመጀመሪያውን የአቡ ሩሚን (አባ ሮሜ) የአማርኛ ቅጅና ግዢ በተመለከተ ስለ ሚስተር ጆዌት ሁኔታ ካተተ በኋላ (ጆዌት ግዢውን ያከናወነው ሰው ነው) እንዲህ ይላል፤

    ". . . ካለፈው ዘገባ እንደሚስተዋለው የግዕዝ መጽሐፍ ቅዱስ በአበሻ ቀሳውስት ላይ ትልቅ የለውጥ ኃይል ምናልባት መፍጠር ቢችልም በአገሪቱ ቋንቋ ማዘጋጀትና ማሰራጨት በሕዝቡ ላይ ብርሃን እንደሚፈነጥቅ መታወቅ አለበት። እንደሚታየው አማርኛና ትግርኛ የሚባሉ ሁለት ትልልቅ ቋንቋዎች አሉ። ሚስተር ጆዌት በአባይ ጉዞው ቋንቋውን የሚያውቀውን ሚስተር ፒርስን ማግኘቱ ይህን ሰው በትርጉሙ ተሳታፊ አድርጎታል። የማርቆስ ወንጌል ቀድሞውኑ በአማርኛና በትግርኛ ተተርጉሞአል። ከዚህ በፊት የተነገረለት የአማርኛ ትርጉም በካይሮ በሚገኘው የፈረንሳይ ቆንስል በኤም አሰሊን (M. Asselin) ስር በጥንቃቄ እየተሠራ ይገኛል። የትርጉሙ ናሙና ገጾች ወደ ኤሮጵ ቢላኩም ወዳልተላከላቸው ሰዎች እጅ በስሕተት ገብቷል። ሥራው አሰሊንን 10 ዓመታት ወጥሮት ቆይቷል። እየተሠራ ያለው በአሰሊን ስር ሆኖ በ[ኢትዮጵያዊ]ዜጋ ነው። በትርጉሙ የዕብራይስጡ ጽሑፍ ከሰብትዋጅንት፥

    4 ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፤ ገጽ 814።

    ዐረብኛ እና ሶርያ ትርጓሜዎች ጋር እና ማብራሪያዎች ጨምረው እየተጠቀሙ ነው። . . . ይህ ትርጉም አሁን ተጠናቅቆአል። ቋንቋው አማርኛ ሲሆን በጎንደር ካለው የመንግሥት ቋንቋ አንድ ሆኖ በአበሻ ፊደል የተጻፈ ነው። . . . የብሪታንያና የውጪ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር የማልታ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበርን ሚስተር ጆዌትን ወኪል አድርጎ ግዢውን እንዲፈጽም በጠየቀው መሠረት ሚስተር ጆዌት የትርጉሙን ጽሑፍ ሊገዛና ለሕትመት ሊያመጣ ወደ ግብጽ ሊሄድ ይዘጋጃል።" 5

    ይህ ከሰፊ የሌሎች አገሮች ዘገባዎችን ከያዘው ሰነድ የተወሰደ ነው። በውጤቱ ሚስተር ዊልያም ጆዌት ከፈረንሳዊው የካይሮ ቆንስል ከዣን-ሉዊ አሰሊን ይህንን የአቡ ሩሚ ትርጉም የሚባለውን ከ9500 ገጾች በላይ የሆነውን ሙሉ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም በ1250 ፓውንድ ገዝቶአል። ግዢው ከተጠናቀቀ በኋላ ጽሑፉ ሳሙኤል ሊ በተባለ ፕሮፌሰር በጥንቃቄ ታይቶ የአማርኛ ፊደል ተቀርጾለት አራቱ ወንጌላት በ1824፥ አዲስ ኪዳን ከአምስት ዓመታት በኋላ በ1829፥ ሙሉው መጽሐፍ ቅዱስ ደግሞ በ1840 ለአንባቢ እንዲቀርብ ታትሞ ተዘጋጀ። አቡ ሩሚ ግብጻዊ ወይም ዐረባዊ አጠራር ሆኖ ትክክለኛ የስማቸው አጠራር አባ ሮሜ ሊሆን ይችላል። በአውሮጳ የሚታወቁት Abu Rumi Habessinus ተሰኝተው ነው። አበሻው አቡ ሩሚ ማለት ነው። የአማርኛ ትርጉም ሥራውን የጀመሩት አስቀድመው አቅደውና አልመው ሳይሆን ከካይሮው የፈረንሳይ ቆንስል 'አጋጣሚ' አገናኝቶአቸው ነው። አቡ ሩሚ አባይን ወንዝ ምንጭ ፍለጋን ያካሄደው የጄምስ ብሩስ አገር አመልካች [እና አማርኛ አስተማሪ] ነበሩ። የጉዞ ፍቅር ያደረባቸው ከዚህ የተነሣ ይሆን? ግብጽን፥ ሶርያን፥ ኢየሩሳሌምን ሕንድን ተጉዘው አይተዋል።

    በካይሮ አቋርጠው ሲያልፉ ድንገት በጠና ታመሙ፤ በሰው አገር። አቡ ሩሚ በዚህን ጊዜ የ45 ወይም የ50 ዓመት ዕድሜ ሰው ናቸው። ይኸኔ ነው አሰሊን ያገኛቸውና ወስዶ ያስታመማቸው። በዚህ ዘመን (1800ዎቹ መጀመሪያ) የአውሮጳ ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ዓይነተኛ ባህርይ ወንጌልን በዓለም ማዳረስና ቃሉን በሰሚዎች ቋንቋ መተርጎም ነበር። አሰሊንም የዚህ ተጋሪ የነበረ ሰውና የቃሉ አጥኚ ነበረ። እያገገሙ ሳሉ አሰሊን ያስተዋለው የሰውየውን የቋንቋ ሊቅነት ነበር። ወደ ኢትዮጵያ ሕዝብ ቋንቋ መጽሐፍ ቅዱስን ለመመለስ ብዙ ተጥሮ አለመሳካቱና አሁን ደግሞ ይህ ዕድል በድንገት የመገኘቱን ሁኔታ በተመለከተ አሰሊን እንዲህ ይገልጠዋል፤ "ይህንን ምስኪን ሽማግሌ ባገኘሁ ጊዜ የተደነቅሁትን መደነቅ ተመልከቱ፤ ይህ ሰው የአገሩ ስነ ጽሑፍ ሊቅ ነው፤ ደግሞም እስከ እስያ ሩቅ ድረስ ዘልቆ የሄደ ተጓዥና የ[ጄምስ] ብሩስ እና የሲር ዊልያም ጆንስ አስተማሪም ነው።"6 ይህን ያነበብኩበት መጽሐፍ ስለ አቡ ሩሚና ስለ ትርጉም ሥራው እንዲህ ይላል፥

    አቡ ሩሚ ከራሱ ቋንቋ በተጨማሪ የግሪክ፥ የዐረብ እና የፋርስ ቋንቋን በማወቁ ለዚህ ትርጉም በጣሙን ብቁ የሆነ ሰው ነው። በቋንቋው መተርጎሙን በአሰሊን መሪነት ወዲያው ተያያዘው። ለአስር ዓመታት በሳምንት ሁለት ቀን ከምንም ሌላ ተግባር ተነጥለው ትርጉሙ የተሠራበትን የዐረብኛውን መጽሐፍ ቅዱስ በማንበብ ጀመሩ። ዐረብኛው ግልጽ ያልሆነባቸውን ቃላት አሰሊን ከምንጩ ቋንቋ፥ ከሶርያ ትርጉም፥ ከሰብትዋጅንት እና ከተላያዩ መዛግብተ ቃላት ይፈታ ነበር። ደግሞም አቡ ሩሚ የሚጠቀምበት የግእዝ ቋንቋ ራሱ ጥሩ መክፈቻ ነበረ። በሥራው የመጀመሪያ ዓመታት አሰሊን በዚህ ሽማግሌ ጓደኛው ትእግሥት በጣም ይደነቅ ነበር። በኋላ ግን እየተረጎሙ ወደ ጳውሎስ መልእክቶች ሲደርሱ የአቡ ሩሚ ፍላጎት መቀዝቀዝ ጀመረ። ይህም የሆነው የሥራው ከባድነት ስላስፈራው ነው። ወደ ኢየሩሳሌምም መሄድ ተመኘ። ይህ ሥራ [ሊያልቅ ተገባድዶ ግን] በጅምር እንዳይቀር ብዙ ጊዜ በወሰደ ልመናና መስዋዕት አሳመነውና ሥራው ቀጠለ። ይህ ሥራ እንደተጠናቀቀ የሆነውን ከዚህ ጋር አያይዞ መናገር አላስፈላጊ አይመስለኝም። ይህ ምስኪን ሰው የትርጉም ሥራው እንደተጠናቀቀ ወዲያውኑ

    5 Proceedings of the Church Mission Society for Africa and the East, Twentieth Year (1819-1820), pp, 111-113. 6 Bagster, Samuel, p. 49. ይህ የሳሙኤል ባግስተር መጽሐፍ በ1848 የታተመና በዚያን ዘመን መጽሐፍ ቅዱስ ወደ ተለያዩ ቋንቋዎች የተመለሱባቸው ታሪኮች ጥርቅም ነው። ከአማርኛው ጋር የትግረ እና የግእዝ ትርጉሞች ኅትመት ታሪክም ተጽፎአል።

  • 6

    ቁጥር ፳፭ -ግንቦት ፪ሺህ ፮ ዓመተ ምሕረት MAY 2014

    የተወደደ ምኞቱን ሊፈጽም ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ። እንደደረሰ ግን በወረርሽኙ ምክንያት ሞተ።7

    አቡ ሩሚ ሥራቸውን በወግ አጠናቀቁና በኢየሩሳሌም በ1819 ሞቱ። ከላይ እንዳልኩትም የእንግሊዝ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ሥራውን ከአሰሊን ገዝቶ የራሱ በማድረግ እንዲታተምና እንዲሰራጭ ሌላ ጥረት አድርጎአል። በ1820 ግዢው ተፈጽሞ በ1821 ወደ እንግሊዝ ከመጣ በኋላ አማርኛን በሚያውቁት የአገሩ ሰዎች ታይቶ በአድናቆት ጸደቀ። ትርጉሙን የፈተሸው ዶ/ር ሳሙኤል ሊ በ1822 ለመጽሐፍ ቅዱስ ኮሚቴው ስለዚህ ሥራ ሲጽፍ፥ "ሥራው በልዩ ችሎታና በጥንቃቄ እንደተሠራ ይታያል፤ በብዙ የምሥራቅ ቋንቋዎች እንደሚታየው ያለ ለአንድ ቃል ብዙ ቃላትን በመጠቀም የመራቀቅ ሊቅነትን ማሳየት በተርጓሚው አልታየም፤ ነገር ግን የተመጠነ፥ ቀላል እና ጤናማ ነው።8 እንደ ናሙና ሆኖ በስፍራው የተቀመጠው ዮሐ. 1፥1-14 እውነትም ይህ ትርጉም 'የተመጠነ፥ ቀላል እና ጤናማ' (precise, easy and natural) እንደሆነ ያሳያል፤

    የአማርኛ (የግእዝ) ፊደላት ተቀርጸው በ1824 ዶ/ር ሊ፥ ሚስተር ጆዌት እና በጊዜው ከመጽሐፍ ቅዱስ ማኅበሩ ጋር እየሠራ የነበረው የምሥራቃውያን ጥናቶች ሊቅ ሚስተር ቶማስ ፔል ፕላት ፈትሸውት ወንጌላት ታተሙ። በ1829 ደግሞ አዲስ ኪዳን፥ በ1840 ብሉይ ኪዳን ታተሙ። በ1842 ሙሉው መጽሐፍ ቅዱስ ለመጀመሪያ ጊዜ በአማርኛ ታተመ። ከዚህ ሙሉ እትም ቀጥሎ የታተመው እስከ ቅርብ ጊዜ እየተሰራጨ የዘለቀው የ1879 እትም የሚባለው ነው። የዚህኛው ቋንቋ ፕላት ከምንጭ ቋንቋዎች ጋር ካመሳከራቸው ነጥቦች ሌላ ከቀድሞው ይልቅ በመጠኑ ለዘብ ያለና የሕዝቡን እንዲመስል መጠነኛ የቃላት ለውጥ ተደርጎበታል።

    ይህን የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም አሳታሚና አሰራጭ አሁንም ቤተ ክህነት ሳትሆን የወንገል ሸክም የከበዳቸው የውጪ ሰዎች እንደሆኑ አንርሳ። ለማስተርጎምና ለማሳተም ብቻ ሳይሆን ለማሰራጨትም የተጣረው ጥረት ቀላል አልነበረም። የእንግሊዝና የውጪ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር 39ኛ ጉባኤ ዘገባ ደግሞ መጽሐፍ ቅዱሱ ከታተመ በኋላ ስለነበረው ስርጭት 3522 መጽሐፎች በግብጽና በአቢሲንያ (የዚያን ዘመን የአበሻ አገር ስም) ላሉት የCMS (Church Missionary Society) የወንጌል መልእክተኞች እንደተላኩ ካተተ በኋላ የተላከላቸውን መጽሐፍ ቅዱሶች ካገኙት አንዱ ክራፍ የተባለው በጊዜው በኢትዮጵያ የነበረ ሚስዮናዊ የጻፈውን በመጥቀስ እንዲህ ይላል፥

    አንኮበር ካለው የምስራቅ አፍሪቃ ሚስዮን ዲሴምበር 14 ቀን 1841 በጄ. ኤል. ክራፍ የተጻፈው ደብዳቤ እንዲህ ይላል፥ "ብዙ የግዕዝና የአማርኛ ብሉይና አዲስ ኪዳኖችን እንዳገኝ ተስፋ አለኝ። ሁሌም በጣም ሩቅ ከሆነ ቦታ የእግዚአብሔርን ቃል ለማግኘት የሚመጡ ብዙ ሰዎች አሉ። ምንም የግዕዝም የአማርኛም መጽሐፍ ቅዱስ ስለሌለኝ ባዶ እጃቸውን ልልካቸው ግድ ሆኖብኛል።" በሌላ በፌብሩዋሪ 28 ቀን 1842 በተጻፈ ደብዳቤ ደግሞ፥ "በ22 ሳጥኖች የተሞሉት

    7 እላይ የተጠቀሰው። 8 እላይ የተጠቀሰው።

    የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱሶችና በርካታ የኢዘንበርግ የመልክዓ ምድርና የክርስትና ጥያቄና መልስ መጽሐፎች በሰላም እንደደረሱኝ የማሳውቃችሁ በደስታ ነው። ስለነዚህ ስጦታዎች የምሕረት ሁሉ አምላክ እግዚአብሔር ይመስገን፤ እናንተንም አመሰግናለሁ። ለዚህች አገር ውጤታማ የወንጌል ሥራ ትልቅ አስተዋጽዖ አላቸውና። . . . ደግሞም የአበሻን ወጣቶች የሚያስተምሩ መምህራን እነዚህን መጽሐፍ ቅዱሶች በምስጋና ተቀብለው ተማሪዎቻቸውን ሊያስተምሩበት ቃል ገብተውልኛል። . . . በማርች 16 ቀን 1842 ከአመድ ዋሻ፥ ሸዋ በተጻፈ ደብዳቤ ደግሞ፥ "ከመነሣቴ በፊት ለመንደሩ ቀሳውስት የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱሶችን አደልኳቸው። እነርሱም ከምስጋና ጋር ተቀበሉት እንጂ በአማርኛ ስለሆነ አልተቃወሙም። አጥብቄ ጠይቄ እንደተረዳሁት ወደዚህ የራቀ የሸዋ ግዛት በጣም ጥቂት መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ነው የደረሰው፤ ስለዚህ ወደ አንኮበር እንደተመለስኩ ጨምሬ ልልክ ወስኛለሁ።"9

    ይህ ዘገባና በጊዜው የChurch Missionary Society የወንጌል መልእክተኛ የነበረው የክራፍ ደብዳቤ የሚያሳየው የአማርኛው ትርጉም ታትሞ ተልኮ በስርጭት ላይ መሆኑንና ተቀባይነቱም የሞቀ እንደነበረ ነው።

    ከወንጌል ሚስዮናውያን እንደ ፈር ቀዳጅ የሚቆጠረው ፒተር ሄይሊንግ በዐፄ ፋሲል ዘመን የገባና ከማስተማር እስከ ሕክምና ከስብከት እስከ ንጉሥ አማካሪነት ድረስ ያገለገለ ሰው ነው። ግብጽ ቆይቶ በ1634 ወደ ኢትዮጵያ የገባው ይህ ሰው የቋንቋ ፈጥኖ ማወቅ ስጦታ የታደለ ሰው ነውና አማርኛን ፈጥኖ መማር ብቻ ሳይሆን አዲስ ኪዳንንም ወደ አማርኛ ለመተርጎም የበቃ መሆኑ ይወሳል። ግን ይህ ቅጅ እምን እንደደረሰ የሚታወቅ አመላካች ነገር አላገኘሁም። ይህ ቅጅ ለሕትመት በቅቶ ኖሮ ቢሆን የመጀመሪያው አዲስ ኪዳን በሆነ ነበር። ፒተር ሄይሊንግ ግብጽ በቆየበት ጊዜ ከካቶሊኮች ጋር ጥብቅ ክርክር ሲከራከር የግብጽን ቤተ ክርስቲያን ለማደስ ደግሞ ሙከራ አድርጎ ነበር። ቀድሞም እርሱን የላከው ወንጌላዊ ድርጅት ዓላማ እና የራሱም አሳብ አዲስ ቤተ ክርስቲያን መትከል ሳይሆን የምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናትን በወንጌል እውቀት ማደስ ነበር።10 ቤተ ክርስቲያን እያለች ቃሉ መሸፈኑና የቃሉ እውቀት በሕዝቡ ዘንድ አለመኖሩ ትልቁ አሳሳቢ ጉዳያቸው ነበር።

    ሄይሊንግ በጊዜው ወደ ኢትዮጵያ የተሾሙትን አቡን አጅቦ ለመምጣት እድል ስላገኘ በአገር ውስጥ ተቀባይነቱ ጠንካራ ሆኖለት ነበር። በመጨረሻ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊ ሃይማኖትን ስሕተቶች በመናገሩ ተሰድዶ ከአገር ቢባረርም ከአገር ከመውጣቱ በፊት በወንጌል አምነው ክርስቶስን ይከተሉ የነበሩና በአገሬው ሕዝብ “መናፍቃን ደቁ ለጀርመን” እየተባሉ የሚጠሩ ደቀ መዛሙርት ነበሩት። ከወንጌል ስብከቱ በተጨማሪ የዮሐንስን ወንጌል መተርጎሙ በውል ተጽፎለታል። ኋላ በኢትዮጵያ የወንጌል መልእክተኛ የነበረው ሳሙኤል ጎባት ይህን ትርጉም በ1830 ማየቱን ጽፎአል።11 ሌላ የሚመሰከርለት ቀዳሚ የአማርኛ ትርጉም እስካልኖረ ድረስ ይህ የፒተር ሄይሊንግ የዮሐንስ ወንጌል ፈር ቀዳጅ ትርጉም ለመሆኑ አጠያያቂ አይሆንም። ከዚህ ጥረትም የምንረዳው ትልቅ እውነት በአገራችን ቋንቋ ወንጌልን እንድንሰማ የጣሩት ከአገራችን ይልቅ የወንጌል ሸክም የከበዳቸው የውጪዎቹ መሆናቸውን ነው።

    በዚሁ ጊዜ በዐፄ ቴዎድሮስ ዘመን ሚስዮናውያን ወንጌልን ለማሮጥ ይለፉና የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስን ለማሰራጨት ይተጉ በነበረ ጊዜ ካህናትና ሊቃውንት ይህንን ጥረት ይጋፉ እንደነበር በዘመኑ የተጻፈ የመጽሔቶች መድብል እንዲህ ይገልጣል። ሳሙኤል ጎባት በኢየሩሳሌም በቅስና ሲያገለግል ሳለ ከኢትዮጵያ የሄደው ሚስተር ፍላድ በኢትዮጵያ ውስጥ ስለነበሩት ሚስዮናውያን ሁኔታ ሳሙኤል ጠይቆት ሲመልስለት ያሉበትን አስቸጋሪ ሁኔታ ሳይደብቅ ከነገረው በኋላ ደስ የሚያሰኘውንም እርምጃ ሲያካፍለው እንዲህ ይላል፥

    9 The Thirty-Ninth Report of the British and Foreign Bible Society, pp. 77-78. 10 http://www.dacb.org/stories/egypt/heyling_peter.html

    11 Encyclopaedia Aethiopica, Vol. 3 pp. 27-28.

  • 7

    ቁጥር ፳፭ -ግንቦት ፪ሺህ ፮ ዓመተ ምሕረት MAY 2014

    ከኢየሩሳሌሙ የአንግሊካኑ ቄስ ከዶ/ር ሳሙኤል ጎባት ዘንድ ጥቂት ሰዎች በመቶ የሚቆጠሩ ለአበሾች የሚታደሉ መጽሐፍ ቅዱሶች ይዘው እንደመጡ ንጉሡ በሰማ ጊዜ ወዲያውኑ የደንብራ [ደንቢያ?] እና ጭልጋ አገረ ገዦችን ከንብረታቸው ሁሉ ጋር ይዘዋቸው እንዲመጡ አዘዘ። ከንጉሡ፥ ከአቡኑ እና ከብዙ ቀሳውስት ጋር ከተነጋገርኩት እንደተገነዘብኩት አቡኑ፥ እጨጌው (የመነኮሳቱ አለቃ) እና ካህናቱ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ እንዳይሰራጭ ይፈልጋሉ። ለብዙዎቹ እንዲያውም የእግዚአብሔር ቃል ሕዝብ በሚረዳው ቋንቋ መተርጎሙ የሚያስገርም ነገር ነው የሆነባቸው። ስለዚህ [ትርጉም] ብዙዎች በንቀት ቃል እየተናገሩ የቤተ ክህነቱን ግእዝ የሚባለውን የኢትዮጵኛ ቋንቋ እያከበሩ ይናገራሉ። ይሁን እንጂ ከብዙ መቶ ካህናት ቋንቋውን [ግእዝን] የሚያውቁ አምስት እንኳ ማግኘት ይቸግራል። አቡኑ አንድ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ እንኳ በስጦታ ለመቀበል እንቢ ብሏል። ንጉሡ ግን የተለየ ነው። ምንም እንኳ በሙያው ወታደር ቢሆንም ከቀሳውስቱ ይልቅ ብሩህ ሰው ነው። መጽሐፍ ቅዱሶችንና [አዲስ] ኪዳኖችን ገጸ በረከት አድርገን አቀረብንለት። ከነዚህ መካከል አራት የግእዝ ዝቅጅዎችም ነበሩበት። ንጉሡ እነዚህን [አራቱን] ወደ ጎን ወረወረና፥ 'ማንም ሊረዳቸው የማይችላቸውን እነዚህን መጻሕፍት ለምን አመጣችሁ? ምን ይጠቅማሉ? የአማርኛዎቹ በጣም ይሻላሉ፤ ሁሉ ሊረዳቸው ይችላልና' አለ።12

    ይህ ጽሑፍ በመቀጠል መጽሐፍ ቅዱስ በመሪዎች፥ በምእመናን፥ በፈላሾች እና በካህናቱም ላይ ስለፈጠረው ተጋቦት እያብራራ የሁለትና የሦስት ቀን የእግር መንገድ ተጉዘው መጽሐፍ ቅዱስ ለመለመንን ስለሚመጡ ሰዎችም ይናገራል። ስለፈጠረው ለውጥም እንዲህ ይላል፥

    . . . ቀድሞ ይጠየፉት የነበሩት ካህናት አሁን አማርኛውን ካነበቡት በኋላ ከግእዙ ይልቅ ይህንን ወደውታል። ንጉሡም የየዕለቱን መዝሙረ ዳዊት እና የጸሎት ምንባቡን የሚያነብበው በአማርኛ ሆኗል። ስለዚህ፥ 'የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ በአበሻ አገር ማሰራጨት ድካም ነው፤ ተነባቢ አይደለም፤ ካህናቱ አይፈልጉትም' አትበሉ። ምናልባት ለጊዜው ውጤታማ አይሆን ይሆናል። በጊዜው ግን ቃሉ በኢሳ. 55፥10-11 እንደተጻፈው የተላከበትን ዓላማ ይፈጽማል። . . . የንጉሡ ንስሐ አባት በአጥቢያ ቤተ ክርስቲያኑ ተሐድሶ ለማድረግ ይመኛል። በየማክሰኞውና በየእሑዱ ከብሉይ ኪዳንና አዲስ ኪዳን ለሕዝቡ በሚገባው ቋንቋ በአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲነበብ አስቦአል። ጸሎቱም እንኳ በአማርኛ እንዲደረግ ምኞት አለው። መልካም አሳቡ ይፈጸም ዘንድና የኢትዮጵያ ጨለማ በብርሃን እንዲተካ ሐሰተኛ መድኅኖቻቸውና ጣዖቶቻቸውም በራሳቸው ቋንቋ በሚያነብቡት በእውነተኛው ብርሃን መጽሐፍ ቅዱስ አማካይነት እንዲወገዱ እግዚአብሔር ንጉሡን በመንፈሱ ይቀባው። እውነተኛው የወንጌል መልእክተኛ መጽሐፍ ቅዱስ ራሱ ነው። ለአበሾች መጽሐፍ ቅዱሶችን ማቅረብ ብዙ የወንጌል መልእክተኞች ከመላክ የተሻለ ሥራ ይሠራል። ነፍሳትን እናጭዳለንና የእግዚአብሔርን ቃል እንዝራ።13

    መጽሐፍ ቅዱስ በሰዎች ሕይወት ውስጥ ስለሚፈጥረው ዘላለማዊ ለውጥ ከአውሮጳውያን ሰዎችም፥ ከላይ በዐፄ ኃይለ ሥላሴም ጥረት እንደተመለከትነው ከካህናቱ ይልቅ ነገሥታቱ ሕዝቡ መጽሐፍ ቅዱስን በገዛ ቋንቋው እንዲያውቅ መጣራቸው አስመስጋኝ ጥረት ነው። ጥረቱ ከሌላው አቅጣጫ ቢሆን ኖሮ ዛሬ ወንጌል ከሰዎች ሕይወት አልፎ የአገሪቱንም መልክ በለወጠ ነበር። የአቡ ሩሚ የአማርኛ ትርጉም ትልቅ ለውጥ በአገሪቱ ክርስትና ላይ መፍጠሩ የታወቀ ነው። ጠቅላላውን ውጤትና ፍሬ የሚያውቀው የቃሉ ባለቤት የሆነው ጌታ ብቻ ሲሆን ከተተረኩልን አንዱ ቃሉን በማጥናትና በቅድስና ለመኖር በመጣር የነበሩ ጥቂት መነኮሳት በሐማሴን በጸዓዘጋ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ግድግዳ ተደብቆ የኖረውን የአቡ ሩሚን የ1940 የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ እትም ባገኙ ጊዜ መንፈሳዊ ጥማታቸው እንደጨመረና ለነፍሳቸው ጥያቄም መልስ ማግኘታቸው ነው። ይህ መቃቃት በኋላ ለኤርትራ ወንጌላዊት ቤተ ክርስቲያን፥ ኋላም የኢትዮጵያ ወንጌላዊት መካነ ኢየሱስ የተጀመረችበት ጅማሬ ነው።

    የወንጌላዊት ቤተ ክርስቲያን መካነ ኢየሱስን ጅማሬ የጻፈው ጉስታቭ አሬን ስለዚህ ሲጽፍ፥ "ይህ በጸዓዘጋ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ግድግዳ ሽንቁር በ1860ዎቹ መጀመሪያ የተገኘው መጽሐፍ ቅዱስ ማንም መኖሩን ሳያውቅ ለብዙ ዓመታት በዚያ ኖሮ ይሆናል። ምናልባት ክራፕፍ ወይም ሙሌይሰን በግንቦት ወይም ሰኔ 1843 የChurch Missionary Society

    12 The Church of England Magazine, Vol. 45 July-December 1858. pp. 316-318. 13 እላይ እንደተጠቀሰው፤ ገጽ 318።

    ከአገር ውስጥ ከመውጣቱ በፊት ካሰራጩት አንዱ ሳይሆንም አይቀርም። ምክንያቱም ፍላድ በ1866 ለደጃዝማች ኃይሉ በግዛቱ እንዲያሰራጭ አራት የበቅሎ ጭነት የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱሶች ከላከበት ከ1866 መጨረሻ በፊት በሐማሴን ምንም የ[አማርኛ] መጽሐፍ ቅዱስ እትም ኖሮ አያውቅም።"14

    የሚነበበው ቃሉ በእውነትም ሥራ ይሠራል። ዛሬ በእጃችን ያሉትን መጽሐፍ ቅዱሶች ስናነብብ የለፉትንና የጣሩትን ሰዎች እያሰብን እግዚአብሔርን ስለ እነርሱ እናመስግን። ሰዎችም ሊረዱት በሚችሉ ቋንቋ ቃሉን እንዲያነብቡና እንዲሰሙ እንጣር፤ ለሚጥሩትም እንጸልይ።

    ዝናብና በረዶ ከሰማይ እንደሚወርድ፥ ምድርን እንደሚያረካት፥ ታበቅልና ታፈራም ዘንድ እንደሚያደርጋት፥ ዘርንም ለሚዘራ እንጀራንም ለሚበላ እንደሚሰጥ እንጂ ወደ ሰማይ እንደማይመለስ፥ ከአፌ የሚወጣ ቃሌ እንዲሁ ይሆናል የምሻውን ያደርጋል የላክሁትንም ይፈጽማል እንጂ ወደ እኔ በከንቱ አይመለስም። ኢሳ. 55፥10-11

    ዘላለም መንግሥቱ © 2014 (፪ሺህ፮) ዕዝራ ስነ ጽሑፍ አገልግሎት / [email protected]

    ዋቤ መጻሕፍት

    Aren, Gustav; Evangelical Pioneers in Ethiopia, Origins of the Evangelical Church Mekane Yesus; Offsetcenter, ab, Stockholm, 1978.

    Bagster, Samuel; The Bible of Every Land, History of the Sacred Scripturein Every Language and Dialect into which Translations have been made; London, 1848.

    Cyclopaedia of Biblical, Theological, and Ecclesiastical Literature, McClintock, John and Strong, James, Harper and Brothers Publishers, New York, 1889.

    Encyclopaedia Aethiopica, Harrassowitz Verlag, Vol. 3 Memminger MedienCentrum, Wiesbaden, Germany, 2007. ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል፥ ቀ ዶ/ር ፥ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም በግዕዝ ቋንቋ፥ ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት፥ አዲስ አበባ፥ 2000 ዓ.ም.

    Proceedings of the Church Mission Society for Africa and the East, Twentieth Year (1819-1820), L. B. Seeley, Printer R. Watt, Crown Court, Temple Bar, London, 1820.

    The Church of England Magazine, Vol. 45 July-December 1858. William Hughes Stationer's Hall Court, Rogerson and Tuxford Printers, London, 1958. The Eightieth Report of the British and Foreign Bible Society, Spottiswood and Co., London, 1884.

    The Thirty-Ninth Report of the British and Foreign Bible Society, Printed by Richard Clay, London, 1843.

    Ullendorf, Edward Ethiopia in the Bible, Oxford, University Press Inc. New York, 1968.

    14 Aren, Gustav, p. 184-5.

  • 8

    ቁጥር ፳፭ -ግንቦት ፪ሺህ ፮ ዓመተ ምሕረት MAY 2014

    የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ

    መዝገበ ቃላት (የዝግጅት ጥረት)

    በዚህ የዕዝራ ስርጭት ባለፉት ዓመታት እየሠራሁ ለቆየሁትና ጌታ ቢፈቅድ በቀጣዮቹ ሦስት ዓመታት ለማጠናቀቅ ስለማስበው ሥራ ላካፍላችሁና በጸሎትም ጌታ ባስቻላችሁ መንገድ ሁሉም አብራችሁን ልትሆኑ እጋብዛለሁ። የዩኒቨርሲቲ ትምህርቴን እንዳጠናቀቅሁ ለጌታ ጥሪ ምላሽ በመስጠት በደብረ ዘይት ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን በወንጌላዊነት እያገለገልኩ ሳለሁ ጌታ የስነ መለኮት ትምህርት በር ከፍቶልኝ በTrinity Western Seminary ተማርኩ። እንደጨረስኩም በኢትዮጵያ ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን ዋና ጽ/ቤት በስነ ጽሑፍ አገልግሎት ዘርፍ ተሰማራሁ። የዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ሥራ ጅማሬ እዚያ ነው።

    ሙከራው እና እስካሁን የሆነው

    የዚህ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ሥራ ሲታቀድ ሰባ ያህል ሰዎች ተሳታፊ ሆነው በ4 ዓመታት፥ ከ1998-2002 (በኛ አቆጣጠር ከ - ዓ. ም.) ተሠርቶ እንዲያልቅ የተወጠነ ዕቅድ ነበር። አሳቡ የሞቀና ልባዊ አቀባበል ከተደረገለት በኋላ የመጀመሪያዎቹ የመሰናዶና የመሠረት ሥራዎች ተከናወኑ። እነዚህም የሥራውን ጠቅላላ ቅርጽ ማውጣት፥ የቃላት ለቀማ ማድረግና ለጸሐፊዎች ምርምር ከአቻ የእንግሊዝኛ ቃል ጋር ማጣበቅ፥ እንዲሁም ለሥራው ጅማሬና በር ከፋች የሚሆኑ ሥልጠናዎች ማዘጋጀትን ያካተቱ ናቸው። ከጥቂት ወራት በኋላ ግን ከገንዘብ እጥረት እና ራዕዩንም ካለመጨበጥ የተነሣ ሥራው ወደቀ።

    የዚያ የተጀመረው መዝገበ ቃላት ሥራ ከትከሻዬ ቢወርድም በልቤ የከበደ ሸክም በመሆኑ ከ1999 ጀምሮ ከሥራ በኋላ ባሉኝ ሰዓቶች ለመሥራት እንደገና ከጅምሩ ሥራውን ቀጠልኩ። ከ2000-2008 ወደ 20% ያህል ሥራ ከተሠራ በኋላ በቀጣይ ዓመታት ጊዜ በሚጠይቁ የተለያዩ ነገሮች (ቤተ ሰብ፥ ሥራ፥ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት) ምክንያት ተንቀርፍፎ በአሁኑ ጊዜ የሥራው 30% ያህል ተጠናቅቆአል። የሥራው ጥራት አጥጋቢ ነው፤ ከ'ሀ' እስከ 'ቀ' አልቆ አሁን 'በ' እየተሠራ ይገኛል። እያንዳንዱ ቃል ከምንጭ የዕብራይስጥ እና የግሪክ ቃላት ጋር እየተቋጠረ ትርጉምና ማብራሪያ ከበቂ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች ጋር እየተደረገለት ተሠርቶአል። በዚህ ምክንያት እንግሊዝኛንም ጨምሮ ከብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት በጣም የላቀ ነው። አሁን እየተሠራ ካለው ከ 'በ' የመጀመሪያ 3 ገጾች ቀጥሎ ባሉት ገጾች አያይዣለሁ።

    በአገራችን ወንጌላዊ ክርስትና በስፋት እጅጉን እያደገ ይሁን እንጂ ጥልቀቱ በጣም ትንሽ መሆኑ ግልጽ ነው። የዚህ አንዱ ችግር ቃሉን በጥልቀት የምናጠናባቸው መሣሪያዎች አለመኖራቸው ነው። የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ከነዚህ አንዱ ነው። ዛሬ በእንግሊዝኛ ወደ ሺህ ያህል የተለያዩ የመጽሐፍ ቅዱስ መዛግብተ ቃላት ይገኛሉ። የኛው ግን ከረጅም ዘመን የክርስትና ታሪካችን አንጻር ሲታይ ለመቁጠርም ያሳፍራል።

    ከበርካታ ዓመታት የመንቀርፈፍ ጉዞ በኋላ ጌታ ቀልቤን ወደዚህ ተጀምሮ ያላለቀ ሥራ አስፈላጊነትና የእርሱ ወደሆነው የሚያስችል ጸጋውም ጭምር ሲያዘነብለው ለማመልክባት ቤተ ክርስቲያን መጋቢዬና ለወንጌል ተልእኮ አስተባባሪ፥ እንዲሁም ለምመግባት ቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎችና ምዕመናን ወደ ኢትዮጵያ በመሄድ በሙሉ ጊዜ ይህንን ሥራ የመቀጠልና የመጨረስ አሳቤን አካፈልኩ። የዚህ ሥራ ጥረት ይህ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት በመጀመሪያ በታቀደው ቅርጽና ጥራት ከ3-4 ዓመት ውስጥ እንዲጠናቀቅ ሲሆን ከዋናው ሥራ ጎን የቋንቋ አርትዖትና የመጽሐፍ ቅዱሳዊ ይዘት ፍተሻ ሥራ ይካሄዳል። እግዚአብሔር ቢፈቅድና ይህ ሥራ ሲያልቅ ግቡና ዓላማው ለክርስቶስ አካል መታነጽና ለእግዚአብሔር ክብር ነው። የመዝገበ ቃላቱ ሥራ ከዚህ በፊት ተጀምሮ የወደቀ ቢሆንም እንደገና ተነሥቶ በትርፍ ጊዜዬ ከአገልግሎትና ከሥራ ጋር፥ ሌሎች በዕዝራ የሚወጡ መጣጥፎችና መጻሕፍትን ከመጻፍም ጋር አሁንም እየሠራሁት አለሁ። ጌታ ቢፈቅድ ከ2015 በኋላ ባሉት 3 ወይም 4 ዓመታት በሙሉ ጊዜ ሥራ ለመጨረስ ተነሥተን የሚጸልዩልን እና ከጎናችን የሚሆኑ ሰዎችን በመጠየቅ ላይ ነን።

    የዚህ ሥራ በረከት ተካፋይ ለመሆን ትወዳላችሁ? የበመጠ መረጃስ ትሻላችሁ?

    ይህንን ሥራ ከኛ ጋር የራሳችሁ ለማድረግና አብራችሁን ልትጠመዱ ብትወድዱ እጅግ ደስ ይለናል። ከምንም ነገር በላይ በጸሎት አስቡን። ለመገናኘትና ስለዚህ ሥራ በግልና በግልጥ ለወያየት ከደስተኞችም በላይ ነን፤ ሥራውን ለማገዝ ወይም ለበለጠ መረጃ ወይም ወደፊት የሥራውን ሂደት ለመከታተል በኢሜይል [email protected] ወይም [email protected] ጠይቁን። ጌታ እንዳስቻላችሁ ልትደግፉን ከወደዳችሁ ድጋፉ በቀጥታ ሳይሆን በምትልከን ቤተ ክርስቲያን በኩል የሚፈጸም ሲሆን አድራሻው ቀጥሎ ይገኛል።

    The Amharic Bible Dictionary

    (Endavor)

    In this issue of Ezra I would like to briefly share with you about the Amharic Bible Dictionary endeavor and plead your prayers and support for its completion.

    After graduating from the University of Asmara, responding to God's call, I served in Debre Zeit, Ethiopia as an evangelist in a local Kale Heywet church. The Lord opened doors for a graduate studies and up on completing my studies at Trinity Western Seminary, I worked in the Ethiopian Kale Heywet Church Head Office. The inception of the Amharic Bible Dictionary was there and then.

    Originally it was intended to be completed by 70 participants in 4 years between 1998 and 2002 I being the editor-in-chief. Unfortunately, lack of funds, and also of vision, doomed the project to fail. After the work was abandoned, because of its weight in my heart, I picked it up and continued single handedly. Currently, about 30% of the work is done at a very slow pace. 'ሀ' to 'ቀ' (the first 9 amharic alphabets) is completed and 'በ' is underway. The first three pages of 'በ' are included as samples in the next pages for viewing. Each entry, not only has an extended definition and ample biblical reference, but also the original Hebrew and Greek equivalents.

    After prayerfully deliberating this worthy project with my home church, we are support raising to do and finish it up in the coming few years. More than anything we need your prayers for us and for this task. If you or someone you know wants to learn more about this work, I am more than happy to share. You can email [email protected] or [email protected] and find out more ways to communicate. As a prayer partner you might want to follow its progress. If the Lord prompts you to support the work you can contact our sending church or its US counterpart at the following addresses:

    Evangelical Free Cchurch of Canada Mission (EFCCM) Box 850 Langley Stn LCD 1 Langley, BC, Canada V3A 8S6 Phone: 1 (877) 305-3322 Email: [email protected] Web: www.efccm.ca/donate In USA ReachGlobal 901E 78th Street Minneapolis, MN. 55420-1300 www.efca.org Phone: 1 (800) 745-2202 ወይም 1 (952) 854-1300

    Zelalem Mengistu

  • 9

    ቁጥር ፳፭ -ግንቦት ፪ሺህ ፮ ዓመተ ምሕረት MAY 2014

    በ፥ ב፥ Β፥ β በለሳን צֳִּרי ጸሪይ ወይም ְִּרי ቢልሻን፤ እንደ መድኃኒት בִּלשָׁן ጽሪይ፤ צ

    የሚቀቡት ከተክል ቅርፊት ላይ የሚገኝ የሚቀመም ሙጫ፤ ዘፍ. 37፥25፤ 43፥11፤ ሕዝ. 27፥17። በኤር. 8፥22፤ 46፥11፤ 51፥8 መድኃኒት እና የሚቀባ መድኃኒት የሚሉት ቃላት በለሳን ከተሰኘው ቃል ጋር አንድ ናቸው። ይህ መድኃኒት ከገለዓድ ጋር መቆራኘቱ በለሳን በዚያ በብዛት ከመገኘቱ ጋር የተያያዘ ነው።

    በለስ תְּאֵן ትኤን፤ תְּאֵנָה ትኤናህ፤ συκῆ ሱኬ፤ σῦκον ሱኮን፤ ፍሬው

    የሚበላ በእስራኤል አገር፥ በግብጽም በብዛት የሚገኝ፥ ከወይን ጋር ብዙ ጊዜ አብሮ የሚጠቀስ የታወቀና የተወደደ የዛፍ ዓይነት፤ ዛፉም ፍሬውም በለስ ይባላሉ፤ ዘኁ. 13፥23፤ 20፥5፤ ዘዳ. 8፥8፤ መሳ. 9፥10-11፤ 1ነገ 4፥25፤ 2ነገ. 18፥31፤ ነህ. 13፥15፤ መዝ. 105፥3፤ መኃ. 2፥13፤ ኢሳ. 36፥16፤ ኢዩ. 1፥7-12፤ ዕን. 2፥12፤ ሐጌ 2፥19፤ ዘካ. 3፥10፤ ማቴ. 7፥16፤ ማር. 11፥13፤ ዮሐ. 1፥49-51።

    በለስ በመጀመሪያ የተጠቀሰ የዛፍ ዓይነት ነው፤ እነ አዳም ዕራቁታቸውን

    ለመሸፈን የበለስን ቅጠሎች ነበር የሰፉት፤ ዘፍ. 3፥7። የበለስ ጥፍጥፍ ለቁስል መድኃኒትነትም ያገለግላል፤ 2ነገ 20፥7፤ ኢሳ. 38፥21። ፍሬው ተለቅሞ ወዲያው ብቻ ሳይሆን ተጠፍጥፎ እንደ ቂጣ ተደርጎም ይበላል፤ 1ሳሙ. 25፥18።

    በምሳሌም መጠባበቅን፥ ምሳ. 27፥18፤ የዘመን መጨረሻን፥ ኢሳ. 34፥4፤ ማር.

    13፥28፤ የትንቢት ፍጻሜን፥ ኤር. 24፥1-8፤ ራእ. 6፥13፤ የማንነትን መለያ፤ ሉቃ. 6፥44፤ ያዕ. 3፥12፤ ውጤትን መጠበቅን፥ ሉቃ. 13፥6-7፤ ለማሳየት ተጠቅሶአል።

    በለዓም בִּלעָם ቢልዓም፤ Βαλαάμ ባላአም፤ በዕብራይስጥ የሕዝብ ያይደለ

    ማለት ነው። በመስጴጦምያ አገር በፋቱራ ይኖር የነበረ ምዋርተኛ ሰው። እስራኤልን ይረግምለት ዘንድ የሞዓብ ንጉሥ ባላቅ ቀጥሮ አስመጣው፤ ታሪኩ በዘኁ. 22-24 ይገኛል። በተጨማሪ፥ ዘዳ. 23፥3-5፤ ኢያ. 24፥9-10፤ ነህ. 13፥2፤ ሚክ. 6፥5 ተጽፎአል። እስራኤልን ለመርገም ከመነሣቱ በፊት እና በሚሄድበት መንገዱ ላይ እግዚአብሔር አስጠነቀቀው፤ የሚናገረውን ብቻ እንዲናገርም ገለጠለት። ሄዶም በመርገም ፈንታ የተባረከውን ሕዝብ ባረከ።

    ይህ ከተደረገ በኋላ በለዓምወደ ስፍራው ተመለሰ፤ ዘኁ. 24፥25። ይህ ወደ

    አገሩ መመለሱ ይመስላል፤ ምናልባት ስፍራው አገሩ ሳይሆን የራሱ መኖሪያ ሊሆን ይችላል። ሄዶም ከሆነ ወዲያውኑ ተመልሶአል፤ ምክንያቱም ቀጥሎ ባለው ምዕራፍ (ዘኁ. 25) የተፈጸመው ኃጢአት በእርሱ ምክንያት መሆኑ በዘኁ. 31፥16 የተጻፈ በመሆኑና እርሱም በኢያሱ ዘመን ከምድያም ነገሥታት ጋር በመገደሉ ነው፤ 31፥8፤ ኢያ. 13፥22። ራእ. 2፥14ም ይህንን ባላቅን ያስተማረውን እኩይ ትምህርቱን ይገልጣል።

    በለዓም በአዲስ ኪዳን እንደ ለዓመጻ ደመወዝ እና ከገንዘብ ሲሉ ሐሰትን

    የሚያስተምሩ የስሕተት አስተማሪዎችና አማኞችን ወደ ሴሰኝነት የሚመሩ አሰናካዮች ምሳሌ ሆኖ ተተቅሶአል፤ 2ጴጥ. 2፥15; ይሁ፣ 11፤ ራእ. 2፥14።

    በለዝ፥ በለዝ እና ያቁም בֹּועַז ቦውዓዝ፤ יָכִין ያኪይን፤ ሰሎሞን ባሠራው

    መቅደስ ወለል አጠገብ ወይም ከቤቱ ፊት የቆሙት ሁለት አዕማድ ስሞች፤ 1ነገ. 7፥15-21፤ 2ዜና 3፥15-17።

    በሉር נֹופֶך ኖውፌክ፤ በካህኑ ደረት ኪስ ከተጠለፉት የከበሩ ድንጋዮች

    አንዱ፤ ዘጸ. 28፥18፤ 39፥11፤ ጢሮስ በዚህ ንግድ በልጽጋ ነበር፤ ሕዝ. 27፥16፤ የጢሮስ ንጉሥ የተባለው ጌጥ ይህም ጭምር ነበረ፤ 28፥13።

    በሊታ፥ ሰው በሊታ אֹכֶלֶת אָָדם ኦኬሌት አዳም፤ ለእስራኤል አሕዛብ

    የሰጡአት የማላገጫ ስም፤ ሕዝ. 36፥13-14። በላሳን בִּלשָׁן ቢልሻን፤ ከዘሩባቤል ጋር ሕዝቡን መርተው ከምርኮ አገር

    ከተመለሱት ሰዎች አንዱ፤ ዕዝ. 2፥2፤ ነህ. 7፥7።

    በላተኛ፥ በላተኞች אֹכֵל ኦኬል፤ φάγος ፋጎስ፤ የሚበላ፤ ለሆዱ ግድ የሚለው፤ መሳ. 14፥14፤ ማቴ. 11፥19፤ ሉቃ. 7፥34። ቲቶ 1፥12 ላይ ያለው ቃል፥ γαστήρ ጋስቴር፤ ቀፈት ማለት ሆኖ ሆዳም፥ አግበስባሽ፥ አልጠግብ ባይ ማለት ነው። በአዲስ ኪዳን እርጉዝ የሚለው ቃልም ከዚህ አንድ ነው፤ ትልቅ ሆድን ለማመልከት ነው።

    በልግ፥ የበልግ ዝናብ ׁמַלקֹוש ማልቆውሽ፤ በበልግ ጊዜ የሚጥል ዝናብ፤

    የኋለኛው ዝናብም ይባላል፤ ዘካ. 10፥1። በምሳሌ በጎ ፈቃድና ሞገስን ማግኘት እንደሆነ ተጠቅሶአል፤ ምሳ. 16፥15።

    በልዳዶስ ד ቢልዳድ፤ ከኢዮብ ሦስት ወዳጆች አንዱ፤ ኢዮ. 2፥11፤ 42፥ בִּלדַּ

    9። ሹሐዊ ተሰኝቶአል፤ ይህ ወገን ኢዮብ ይኖር ከነበረበት ከምሥራቅ ሕዝቦች አንድ ወገን ሳይሆን አይቀርም። በልዳዶስ በመጽሐፈ ኢዮብ ውስጥ ሦስት ጊዜዎች በኢዮብ ላይ የወቀሳ ንግግር አድርጎአል፤ ኢዮ. 8፥1-22፤ 18፥1-21፤ እና 25፥1-6። ከንግግሮቹ፥ በተለይም ከመጀመሪያዎቹ ሁለት ንግግሮቹ መገንዘብ እንደሚቻለው የዚህ ሰው መረዳት ኢዮብ ልጆቹ የሞቱት በበደላቸው እንደሆነ፥ ንጹሕና ቅን ቢሆን ኖሮ እግዚአብሔር እንደሚፈጥንለት፥ እየደረሰበት ያለው ስቃይ ኃጢአተኞች የሚቀጡበት መሆኑን ነው።

    በሎታ תֹּותָח ቶውታኽ፤ ወርውረው ወይም ሰንዝረው የሚመቱበት መምቻ

    ወይም መውጊያ፤ ኢዮ. 41፥21። በረሃ מִדבָּר ሚድባር፤ שְׁמָמָה ሽማማህ שִׁמָמָה ወይም ሺማማህ፤ יְשִׁימֹון

    ይሺይሞውን፤ בַּתּתָּה ባታህ፤ עָיֵף אֶֶרץ አዬፍ ኤሬጽ፤ ִּיָה ጺያህ፤ צἔρημος ኤሬሞስ፤ ምድረ በዳ፤ የደረቀና የተጠማ፥ እርጥበትና ውኃ የሌለበት፥ ለእርሻና ለእርባታ የማይስማማ ባዶ ምድር፤ ዘሌ. 16፥22፤ ኢያ. 8፥28፤ 1ሳሙ. 13፥18፤ 2ሳሙ. 16፥2፤ መዝ. 106፥14፤ ኢሳ. 7፥19፤ 32፥2፤ ሕዝ. 6፥14፤ ኢዩ. 2፥3፥20፤ 3፥19፤ ሶፎ. 2፥13፤ ሉቃ. 15፥4፤ ማቴ. 24፥26፤ ሐዋ. 13፥18፤ ራእ. 12፥6፥14፤ 17፥3። በአንዳንድ ስፍራ በረሃ የተሰኘው ሰፊ ጠፍ ሜዳ (שֶָׂדה שַָׂדי ሳዴህ ወይም ሳዳይ) ነው፤ ለምሳሌ፥ ዘኁ. 21፥20፤ 1ሳሙ. 30፥11፤ መዝ. 78፥43።

    በበረሃ የሚኖሩ እንስሳት አንዳንድ ጊዜ በመኖሪያቸው ይጠራሉ፤ ለምሳሌ፤

    የበረሃ ፍየል፤ ዘዳ. 14፥5፤ 1ሳሙ. 24፥2፤ 1ነገ. 4፥23፤ ኢዮ. 39፥1፤ የበረሃ አህያ፤ ኢዮ. 39፥6፤ መዝ. 104፥11፤ የበረሃ ተኩላ፤ ኤር. 5፥6። የበረሃ ተክሎችና መብልም እንደዚያ ይጠራል፤ ለምሳሌ፥ የበረሃ ቅል፥ 2ነገ. 4፥39፤ የበረሃ ማር፥ ማቴ፣ 4፥3፤ ማር. 1፥6፤ የበረሃ ወይራ፤ ነህ. 8፥ 14-15፤ ሮሜ 11፥17፥24። እነዚህን ቃላት በስፍራቸው ተመልከቱ። በተጨማሪ ምድረ በዳን ተመልከቱ።

    በረቅ שֶֶׂרד ሴሬድ፤ የተለካ ነገርን ወግቶ ወይም ጭሮ ቦታውን ወይም

    ስፍራውን ማመልከቻ መጫሪያ መሣሪያ፤ ኢሳ. 44፥3። በረት אֲוֵָרה አዌራህ፤ אֹוהֶל ኦውኼል፤ גְֵּדָרה ግዴራህ፤  מִכלָאָה

    ሚክላህ ወይም ሚክላአህ፤ αὐλή ኦሌይ፤ በውጪ የሚገኝ የተቀጠረ מִכלָהወይም የተገደገደ የከብቶች ማሳደሪያና መጠበቂያ፥ 2ዜና. 14፥15፤ 32፥28፤ ዕን. 3፥17፤ ሶፎ. 2፥6፤ ዮሐ. 10፥1። በተጨማሪ ጋጥን እና ግርግምን ተመልከቱ።

    በረኛ  שֹׁועֵר ሾኤር፤ ֽף ሻማር ኻሳፍ፤ θυρωρός ቱሮሮስ፤ የበር שֹׁמֵר הַסַּ

    ዘበኛ ወይም ጠባቂ፥ የበር ከፋችና ዘጊ፤ 1ዜና 9፥21፤ 2ዜና 31፥14፤ ኤር. 35፥4፤ ማር. 13፥34፤ ዮሐ. 10፥3፤ 18፥16-17።

    በረከት בַָּרך ባራክ፤ בְָּרכָה ብራካህ፤ εὐλογία ኤውሎጊያ፤ ምንጩ

    ከእግዚአብሔር የሆነ ማናቸውም ምድራዊ፥ ቁሳዊ፥ ሥጋዊ፥ መንፈሳዊ፥ ሰማያዊ በጎ ነገር ሁሉ በረከት ነው። ይህ ቃል የቁጥርና የመጠን ብዛትንም ያመለክታል፤ ዘፍ. 12፥2፤ 22፥17፤ 39፥5፤ ዘጸ. 32፥29፤ ዘዳ. 11፥26፤ 2ሳሙ. 7፥29፤ ሕዝ. 44፥39፤ ሚል. 3፥10፤ 2ቆሮ. 9፥5-6፤ ገላ. 3፥14፤ ኤፌ. 1፥3፤ ዕብ. 6፥7፤ 1ጴጥ. 3፥9፤ ያዕ. 3፥10። የዚህ በረከት መተላለፊያ መሆንም በረከት መሆን ይባላል፤ ዘፍ. 12፥2፤ ኢሳ. 19፥ 24-25፤ ዘካ. 8፥13። ለሌላው

  • 10

    ቁጥር ፳፭ -ግንቦት ፪ሺህ ፮ ዓመተ ምሕረት MAY 2014

    የሚተላለፍ፥ የሚሰጥ ስጦታ ወይም መልካም ነገርም በረከት ነው፤ 1ሳሙ. 30፥26።

    በዘፍ. 45፥18-23 በረከት የሚለው ቃል (טּוּב ቱውብ ወይም טֹּוב ቶውብ) መልካም ነገር ሁሉ ማለት ነው፤ ነህ. 9፥36፤ ኢዮ. 20፥21፤ ምሳ. 65፥4፤ ኢሳ. 1፥19፤ 55፥2፤ ኤር. 2፥7፤ ሆሴ. 3፥5። በአዲስ ኪዳንም መልካም ነገር (ἀγαθός) ወይም ብዙ መልካም ነገር (πολλὰ ἀγαθὰ) በረከት ተሰኝቶአል፤ ሉቃ. 12፥19፤ በጌታ ራት መታሰቢያ ቅዱሳን የሚወስዱት ጽዋ የበረከት ጽዋ ተሰኝቶአል፤ 1ቆሮ. 10፥16።

    በዘፍ. 27፥35 በረከት የተሰኘው ይስሐቅ ያዕቆብን የባረከው ቃል ነው፤

    በረከት የምንቀበለው ተጨባጭ ነገር ብቻ ሳይሆን የተስፋ ቃልና ለሌላውና ለእግዚአብሔርም ጭምር የምንናገረው መልካም ቃልም ነው፤ ዘፍ. 27፥36-38፤ 49፥25፤ ዘዳ. 33፥1፥23፤ ራእ. 5፥12-13፤ 7፥12። መልካም ቃልን መናገር መባረክ ወይም በረከትን መናገር ለመሆኑ በተጨማሪ ባረከ፥ መባረክን ተመልከቱ።

    በረከት፥ የበረከት ሸለቆ עֵמֶק בְָּרכָה ዔሜቅ ብራካህ፤ የበረከት ሸለቆ

    ማለት ነው። በኢዮሳፍጥ ዘመን ይሁዳን ሊወጉ የመጡ ሞዓባውያን፥ አሞናውያንና ምዑናውያን የተሸነፉበትና የተመቱበት ብቻ ሳይሆን የይሁዳ ሰዎች ምርኮን የበዘበዙበት ሸለቆ፤ 2ዜና. 20፥26። የበረከት ሸለቆ የተባለውም ስለዚህ ነው። ይህ ሸለቆ በቁ. 16 የተጠቀሰው የቀድሞ ስሙ ሌላ የነበረ በይሩኤል ምድረ በዳ ፊት ለፊት የሚገኝ ስፍራ ነው።

    በረዶ בָָּרד ባራድ፤ ֶׁלֶגש ሼሌግ፤ תְּלַג ትላግ፤ χιών ኪዮን፤ χάλαζα

    ካላዛ፤ እንደ ዝናም የሚወርድ ቀዝቃዛና ጠጣር ውኃ፤ እንደ ዝናም ወይም ለቅጣት ይወርዳል፤ ዘጸ. 9፥19-34፤ ኢያ. 10፥11፤ ኢዮ. 38፥22፥29፤ ሐጌ 2፥17፤ ራእ. 11፥19፤ 16፥21። አመዳይም ይባላል፤ ኢሳ. 1፥18።

    በምሳሌ የቆዳ ነጭ መሆንን፤ ዘጸ. 4፥6፤ 2ነገ. 5፥27፤ ከሰማይ የ�